2 ስለዚህ ዳዊትና አብረውት ያሉት ስድስት መቶ ሰዎች ተነሥተው የጌት ንጉሥ ወደ ሆነው ወደ አሜህ ልጅ ወደ አንኩስ ሄዱ።
3 ዳዊትና ሰዎቹ በጌት በአንኩስ ዘንድ ተቀመጡ፤ እያንዳንዱ ሰው ከቤተ ሰቡ ጋር ነበረ፤ ዳዊትም ከሁለቱ ሚስቶቹ ጋር፣ ከኢይዝራኤላዊቷ ከአኪናሆምና የናባል ሚስት ከነበረችው ከቀርሜሎሳዊቷ አቢግያ ጋር ነበር።
4 ሳኦልም፣ ዳዊት ወደ ጌት እንደ ሸሸ በሰማ ጊዜ፣ እርሱን ማሳደዱን ተወ።
5 ከዚያም ዳዊት አንኩስን፣ “በፊትህ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ፣ በአገሪቱ ካሉት ከተሞች በአንዲቱ እኖር ዘንድ ስፍራ ይሰጠኝ፤ ስለ ምን አገልጋይህ ካንተ ጋር በንጉሥ ከተማ ይቀመጣል?” አለው።
6 ስለዚህ በዚያ ዕለት አንኩስ ጺቅላግን ሰጠው፤ ጺቅላግም ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የይሁዳ ነገሥታት ይዞታ ሆነች።
7 ዳዊት በፍልስጥኤማውያን ምድር አንድ ዓመት ከአራት ወር ተቀመጠ።
8 በዚያ ጊዜም ዳዊትና ሰዎቹ ወጥተው ጌሹራውያንን፣ ጌርዛውያንንና አማሌቃውያንን ወረሩ። እነዚህ ሕዝቦች ከጥንት ጀምሮ፣ እስከ ሱርና እስከ ግብፅ ባለው ምድር ላይ ይኖሩ ነበር።