ሰቆቃወ 2:6-12 NASV

6 ማደሪያውን እንደ አትክልት ስፍራ ባዶ አደረገ፤መሰብሰቢያ ስፍራውን አፈረሰ፤ እግዚአብሔር ጽዮንን፣ዓመት በዓላቶቿንና ሰንበታቷን እንድትረሳ አደረጋት፤በጽኑ ቍጣው፣ንጉሡንና ካህኑን እጅግ ናቀ።

7 እግዚአብሔር መሠዊያውን ናቀ፤መቅደሱንም ተወ፤የቤተ መንግሥቶቿን ቅጥሮች፣ለጠላት አሳልፎ ሰጠ፤በዓመት በዓል ቀን እንደሚደረገው በእግዚአብሔር ቤት በኀይል ጮኹ።

8 በጽዮን ሴት ልጅ ዙሪያ ያለውን ቅጥር፣ እግዚአብሔር ለማፍረስ ወሰነ፤የመለኪያ ገመድ ዘረጋ፤ከማጥፋትም እጆቹን አልሰበሰበም፤ምሽጎችና ቅጥሮች እንዲያለቅሱ አደረገ፤በአንድነትም ጠፉ።

9 በሮቿ ወደ ምድር ሰመጡ፤የብረት መወርወሪያዎቻቸውን ሰባበረ፤ አጠፋቸውም፤ንጉሥዋና መሳፍንቶቿ በአሕዛብ መካከል ተማርከው ተሰደዋል፤ሕጉ ከእንግዲህ አይኖርም፤ነቢያቶቿም ከእንግዲህ፣ ከእግዚአብሔር ራእይ አያገኙም።

10 የጽዮን ሴት ልጅ ሽማግሌዎች፣በምድር ላይ በዝምታ ተቀምጠዋል፤በራሳቸው ላይ ትቢያ ነሰነሱ፤ማቅም ለበሱ፤የኢየሩሳሌም ወጣት ሴቶች፣ራሳቸውን ወደ ምድር ዝቅ አደረጉ።

11 ዐይኔ በለቅሶ ደከመ፤ነፍሴ በውስጤ ተሠቃየች፤ልቤም በሐዘን ፈሰሰች፣በከተማዪቱ መንገዶች ላይ፣ሕዝቤ ተደምስሰዋልና፤ልጆችና ሕፃናት ደክመዋልና።

12 በከተማዪቱ መንገዶች ላይ፣እንደ ቈሰሉ ሰዎች ሲደክሙ፣በእናታቸው ክንድ ላይ፣ነፍሳቸው በመውጣት ላይ ሳለች፣“እንጀራና የወይን ጠጅ የት አለ?”እያሉ እናቶቻቸውን ይጠይቃሉ።