1 ሳሙኤል 9:11-17 NASV

11 በከተማዪቱ መዳረሻ ያለውን ኰረብታ በመውጣት ላይ ሳሉ፣ ውሃ ለመቅዳት የሚወጡ ልጃገረዶችን አግኝተው፣ “ባለ ራእዩ እዚህ ነውን?” ሲሉ ጠየቁ።

12 እነርሱም እንዲህ ሲሉ መለሱላቸው፤ “አዎን አለ፤ እነሆ፤ ከፊታችሁ ነው፤ ፈጠን በሉ፤ ሕዝቡ በማምለኪያው ኰረብታ ላይ መሥዋዕት ስለሚያቀርብ፣ ወደ ከተማችን ገና ዛሬ መምጣቱ ነው፤

13 ወደ ከተማዪቱም በገባችሁ ጊዜ፣ ለመብላት ወደ ማምለኪያው ኰረብታ ከመውጣቱ በፊት ታገኙታላችሁ። መሥዋዕቱን እርሱ መባረክ ስላለበት፣ እርሱ እስኪመጣ ድረስ ሕዝቡ መብላት አይጀምርም፤ ከዚያ በኋላ የተጋበዘው ሕዝብ ይበላል፤ አሁኑኑ ውጡ፤ ወዲያው ታገኙታላችሁ።”

14 እነርሱም ወደ ከተማዪቱ ወጡ፤ ወደ ከተማዪቱም በመግባት ላይ ሳሉ፣ እነሆ፤ ሳሙኤል ወደ ማምለኪያው ኰረብታ ለመውጣት እነርሱ ወዳሉበት አቅጣጫ መጣ።

15 ሳኦል ከመምጣቱ ከአንድ ቀን በፊት እግዚአብሔር ለሳሙኤል ይህንን እንዲህ ሲል ገልጦለት ነበር፤

16 “ነገ በዚህ ጊዜ ከብንያም ምድር አንድ ሰው ወደ አንተ እልካለሁ፤ በሕዝቤ በእስራኤል ላይ መሪ እንዲሆን ቅባው፤ እርሱም ሕዝቤን ከፍልስጥኤማውያን እጅ ይታደጋል። እነሆ፤ ሕዝቤን ከላይ ተመልክቻለሁ፤ ጩኸቱ ከእኔ ዘንድ ደርሶአልና።”

17 ሳሙኤል ሳኦልን ባየው ጊዜ እግዚአብሔር፣ “ያ የነገርሁህ ሰው እነሆ፤ እርሱም ሕዝቤን ይገዛል” አለው።