ዕንባቆም 2:4-10 NASV

4 “እነሆ፤ እርሱ ታብዮአል፤ምኞቱ ቀና አይደለም፤ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል።

5 በእርግጥ የወይን ጠጅ አታሎታል፤ትዕቢተኛ ነው፤ ከቶ አያርፍም፤እንደ ሲኦል ስስታም ነው፣እንደ ሞት ከቶ አይጠግብም፤ሕዝቦችን ለራሱ ይሰበስባል፤ሰዎችንም ሁሉ ማርኮ ይወስዳል።

6 “ታዲያ በእንደዚህ ዐይነቱ ሰው ላይ በማፌዝና በመዘበት እንዲህ እያሉ ሁሉም አይሣለቁበትምን?“የተሰረቀውን ሸቀጥ ለራሱ ለሚያከማች፣ራሱን በዐመፅ ባለጠጋ ለሚያደርግ ወዮለት!ይህ የሚቀጥለውስ እስከ መቼ ነው?”

7 ባለ ዕዳ ያደረግሃቸው ድንገት አይነሡብህምን?ነቅተውስ አያስደነግጡህምን?በእጃቸውም ትወድቃለህ።

8 አንተ ብዙ ሕዝብ ስለ ዘረፍህ፣የተረፉት ሕዝቦች ይዘርፉሃል፤የሰው ደም አፍሰሃልና፤አገሮችንና ከተሞችን፣ በውስጣቸው የሚኖሩትን ሁሉ አጥፍተሃል።

9 “በተጭበረበረ ትርፍ መኖሪያውን ለሚገነባ፣ከጠላት እጅ ለማምለጥ፣ቤቱን በከፍታ ላይ ለሚሠራ ወዮለት!

10 የብዙ ሰዎች ነፍስ እንዲጠፋ አሢረሃል፤በገዛ ቤትህ ላይ ውርደትን፣ በራስህም ላይ ጥፋትን አምጥተሃል።