2 ዜና መዋዕል 24:14-20 NASV

14 ከጨረሱም በኋላ ቀሪውን ገንዘብ ወደ ንጉሡና ወደ ዮዳሄ አመጡ፤ በገንዘቡም የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ዕቃዎች ማለትም ለአገልግሎትና ለሚቃጠል መሥዋዕት የሚውሉ ዕቃዎች እንደዚሁም ጭልፋዎችና ሌሎች የወርቅና የብር ዕቃዎችም ተሠሩ። ዮዳሄ በሕይወት በነበረበት ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሚቃጠል መሥዋዕት ዘወትር ይቀርብ ነበር።

15 ዮዳሄ ሸምግሎ ዕድሜ ከጠገበ በኋላ በመቶ ሠላሳ ዓመቱ ሞተ።

16 እርሱም በእስራኤል ውስጥ ለእግዚአብሔርና ለቤተ መቅደሱ መልካም ሠርቶአልና በዳዊት ከተማ በነገሥታቱ መቃብር ተቀበረ።

17 ከዮዳሄ ሞት በኋላ የይሁዳ ሹማምት መጥተው ለንጉሡ ታማኝነታቸውን ገለጡ፤ ንጉሡም አዳመጣቸው።

18 እነርሱም የአባቶቻቸውን አምላክ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ትተው፣ የአሼራን ዐምዶችና ጣዖታትን አመለኩ፤ በበደላቸውም ምክንያት የእግዚአብሔር ቊጣ በይሁዳና በኢየሩሳሌም ላይ መጣ።

19 ወደ እግዚአብሔር ይመልሷቸው ዘንድ እርሱ ነቢያቱን ወደ ሕዝቡ ሰደደ፤ ነቢያቱም መሰከሩባቸው፤ እነርሱ ግን አላዳመጡም።

20 የእግዚአብሔርም መንፈስ በካህኑ በዮዳሄ ልጅ በዘካርያስ ላይ መጣ፤ እርሱም በሕዝቡ ፊት ቆሞ፣ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ለምን ትተላለፋላችሁ? አይሳካላችሁም፤ እናንተ እግዚአብሔርን ስለ ተዋችሁት እርሱም ትቶአችኋል” አላቸው።