2 ዜና መዋዕል 25:2-8 NASV

2 እርሱም በእግዚአብሔር ፊት መልካም ነገር አደረገ፤ ነገር ግን በፍጹም ልቡ አልነበረም።

3 መንግሥቱን ካጸና በኋላ፣ ንጉሥ የነበረውን አባቱን የገደሉትን ሹማምት በሞት ቀጣቸው።

4 እግዚአብሔር በሙሴ መጽሐፍ በተጻፈው ሕግ “ሰው ሁሉ በገዛ ኀጢአቱ ይሙት እንጂ ወላጆች ስለ ልጆቻቸው አይገደሉ፤ ልጆችም ስለ ወላጆቻቸው አይገደሉ” ብሎ ባዘዘው መሠረት አደረገ እንጂ ልጆቻቸውን አልገደለም።

5 አሜስያስ የይሁዳን ሕዝብ በአንድነት ሰብስቦ፣ እንደየቤተ ሰቡ በሻለቆችና በመቶ አለቆች በመደልደል በመላው ይሁዳና በብንያም መደባቸው። ከዚያም ዕድሜያቸው ሃያና ከሃያ በላይ የሆናቸውን ሰብስቦ፣ ለውትድርና አገልግሎት ብቁ ሆነው ጋሻና ጦር መያዝ የሚችሉ ሦስት መቶ ሺህ ሰዎች አገኘ።

6 እንዲሁም በመቶ መክሊት ጥሬ ብር አንድ መቶ ሺህ ተዋጊዎች ከእስራኤል ቀጠረ።

7 ነገር ግን አንድ የእግዚአብሔር ሰው ወደ እርሱ መጥቶ እንዲህ አለው፤ “ንጉሥ ሆይ፤ እግዚአብሔር ከእስራኤልም ሆነ ከማናቸውም የኤፍሬም ሕዝብ ጋር አይደለምና፣ እነዚህ የእስራኤል ወታደሮች ከአንተ ጋር አይዝመቱ።

8 ሄደህ ጦርነቱን በቈራጥነት ብትዋጋም እንኳ፣ የመርዳትና የመጣል ኀይል ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለ ሆነ እግዚአብሔር በጠላቶችህ ፊት ይጥልሃል።”