2 ዜና መዋዕል 25:5-11 NASV

5 አሜስያስ የይሁዳን ሕዝብ በአንድነት ሰብስቦ፣ እንደየቤተ ሰቡ በሻለቆችና በመቶ አለቆች በመደልደል በመላው ይሁዳና በብንያም መደባቸው። ከዚያም ዕድሜያቸው ሃያና ከሃያ በላይ የሆናቸውን ሰብስቦ፣ ለውትድርና አገልግሎት ብቁ ሆነው ጋሻና ጦር መያዝ የሚችሉ ሦስት መቶ ሺህ ሰዎች አገኘ።

6 እንዲሁም በመቶ መክሊት ጥሬ ብር አንድ መቶ ሺህ ተዋጊዎች ከእስራኤል ቀጠረ።

7 ነገር ግን አንድ የእግዚአብሔር ሰው ወደ እርሱ መጥቶ እንዲህ አለው፤ “ንጉሥ ሆይ፤ እግዚአብሔር ከእስራኤልም ሆነ ከማናቸውም የኤፍሬም ሕዝብ ጋር አይደለምና፣ እነዚህ የእስራኤል ወታደሮች ከአንተ ጋር አይዝመቱ።

8 ሄደህ ጦርነቱን በቈራጥነት ብትዋጋም እንኳ፣ የመርዳትና የመጣል ኀይል ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለ ሆነ እግዚአብሔር በጠላቶችህ ፊት ይጥልሃል።”

9 አሜስያስም የእግዚአብሔርን ሰው፣ “ታዲያ ለእነዚህ ለእስራኤል ወታደሮች የከፈልኩት መቶ መክሊት እንዴት ይሁን?” ሲል ጠየቀው የእግዚአብሔርም ሰው፣ “እግዚአብሔር ከዚህ አብልጦ ሊሰጥህ ይችላል” ሲል መለሰለት።

10 ስለዚህ አሜስያስ ከኤፍሬም ወደ እርሱ የመጡትን ወታደሮች ወደየመኖሪያ ስፍራቸው አሰናበታቸው። እነርሱም በይሁዳ ላይ ክፉኛ ተበሳጭተው ነበርና በታላቅ ቊጣ ወደ መኖሪያ ስፍራቸው ተመለሱ።

11 አሜስያስም ኃይሉን በሚገባ አደራጅቶ ሰራዊቱን ወደ ጨው ሸለቆ መራ፤ በዚያም ዐሥር ሺህ የሴይር ወታደሮችን ገደለ።