1 በእምነቱ ደካማ የሆነውን ሰው፣ አከራካሪ በሆኑ ጒዳዮች ላይ በአቋሙ ሳትፈርዱበት ተቀበሉት።
2 የአንድ ሰው እምነቱ ማንኛውንም ነገር እንዲበላ ይፈቅድለታል፤ በእምነቱ ያልጠነከረው ሌላው ሰው ግን አትክልት ብቻ ይበላል።
3 ማንኛውንም የሚበላ የማይበላውን አይናቅ፤ የማይበላውም፣ የሚበላውን አይኰንን፤ እግዚአብሔር ተቀብሎታልና።
4 ሌላውን በሚያገለግል ላይ የምትፈርድ አንተ ማን ነህ? እርሱ ቢወድቅ ወይም ቢቆም ለጌታው ነው፤ ጌታ ሊያቆመው ስለሚችልም ይቆማል።
5 አንድ ሰው አንዱን ቀን ከሌላው የተሻለ ቅዱስ አድርጎ ይቈጥራል፤ ሌላው ደግሞ ቀኖች ሁሉ እኩል እንደሆኑ ያስባል። እያንዳንዱ የራሱን ውሳኔ ልብ ብሎ ይወስን።
6 አንድን ቀን ከሌላው የተለየ አድርጎ የሚያስብ ሰው፣ እንዲህ የሚያደርገው ለጌታ ብሎ ነው፤ ሥጋ የሚበላውም ለጌታ ብሎ ይበላል፤ ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀርባልና። የማይበላም ለጌታ ሲል አይበላም፤ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ያቀርባል።