2 በኢየሩሳሌም ተቀምጦም ሦስት ዓመት ገዛ። እናቱ ሚካያ ትባላለች፤ እርሷም የገብዓ ተወላጅ የኡርኤል ልጅ ነበረች።በአብያና በኢዮርብዓምም መካከል ጦርነት ነበር።
3 አብያ አራት መቶ ሺህ ብርቱ ተዋጊዎች ይዞ ዘመተ፤ ኢዮርብዓምም ስምንት መቶ ሺህ ብርቱ ተዋጊዎች ይዞ በመውጣት ጠበቀው።
4 አብያ በኰረብታማው በኤፍሬም አገር በጽማራይም ተራራ ላይ ቆሞ፣ እንዲህ አለ፤ “ኢዮርብዓምና እስራኤል ሁሉ አድምጡኝ!
5 የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ዳዊትና ዘሮቹ በእስራኤል ላይ ለዘላለም እንዲነግሡ በጨው ኪዳን የሰጣቸው መሆኑን አታውቁምን?
6 የዳዊት ልጅ የሰሎሞን ባሪያ የነበረው የናባጥ ልጅ ኢዮርብዓም ግን በጌታው ላይ ዐመፀ።
7 የሰሎሞን ልጅ ሮብዓም ገና ሕፃን ሳለ፣ ምንም ማድረግ በማይችልበትና እነርሱንም ለመቋቋም አቅሙ በማይፈቅድለት ጊዜ የማይረቡ ጥቂት ወሮበሎች በዙሪያው ተሰበሰቡበት፣ በረቱበትም።
8 “አሁንም እናንተ በዳዊት ዘርዐ-ትውልድ እጅ ያለውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ልትቋቋሙ አስባችኋል። በእርግጥም በሰራዊት ረገድ እጅግ ብዙ ናችሁ፤ አማልክቶቻችሁ ይሆኑ ዘንድ ኢዮርብዓም የሠራቸውንም የወርቅ ጥጆች ይዛችኋል።