2 ዜና መዋዕል 30:18-24 NASV

18 ምንም እንኳ ከኤፍሬም፣ ከምናሴ፣ ከይሳኮርና ከዛብሎን ከመጡት አብዛኛዎቹ ራሳቸውን ያላነጹ ቢሆንም ከተጻፈው ትእዛዝ ውጭ ፋሲካውን በሉ። ሕዝቅያስ ግን እንዲህ ሲል ጸለየ፤ “ቸሩ እግዚአብሔር ሆይ፤ ይቅር በላቸው፤

19 ምንም እንኳ በመቅደሱ ሥርዐት መሠረት የነጹ ሆነው ባይገኙም የአባቶቻቸው አምላክ የሆነውን እግዚአብሔር አምላካቸውን ለመፈለግ ልባቸውን የሚያዘጋጁትን ሁሉ ይቅር በላቸው።”

20 እግዚአብሔርም ሕዝቅያስን ሰማው፤ ሕዝቡንም ፈወሰ።

21 ሌዋውያኑና ካህናቱ በእግዚአብሔር የዜማ ዕቃ ታጅበው፣ በየዕለቱ ለእግዚአብሔር እየዘመሩ፣ በኢየሩሳሌም የነበሩት እስራኤላውያን የቂጣን በዓል በታላቅ ደስታ ለሰባት ቀን አከበሩ፤

22 ሕዝቅያስም በእግዚአብሔር አገልግሎት አስተዋዮች የነበሩትን ሌዋውያን ሁሉ በንግግሩ አበረታታ። ሰባቱንም ቀን የተወሰነላቸውን ድርሻ እየበሉና የኅብረት መሥዋዕቱንም እያቀረቡ የአባቶቻቸውን አምላክ እግዚአብሔርን አመሰገኑ።

23 ጉባዔውም ሁሉ በተከታዩ ሰባት ቀን በዓሉን እንደ ገና ለማክበር ተስማሙ፣ ስለዚህ በዓሉን ለሰባት ተጨማሪ ቀን በታላቅ ደስታ አከበሩ።

24 የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስ አንድ ሺህ ወይፈን፣ ሰባት ሺህ በግና ፍየል ለጉባኤው ሰጠ፤ ሹማምቱም እንደዚሁ አንድ ሺህ ወይፈን፣ ዐሥር ሺህ በግና ፍየል ሰጡ። እጅግ ብዙ ካህናትም ራሳቸውን ቀደሱ።