ዘዳግም 26:8-14 NASV

8 ከዚህ የተነሣ እግዚአብሔር (ያህዌ) በብርቱ እጅና በተዘረጋች ክንድ፣ በታላቅ ድንጋጤ፣ በታምራዊ ምልክትና በድንቅ ከግብፅ አወጣን።

9 ወደዚህ ስፍራ አመጣን፤ ማርና ወተት የምታፈሰውን ይህችን ምድር ሰጠን፤

10 አሁንም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ “እነሆ፣ አንተ የሰጠኸኝን የምድሪቱን በኵራት አምጥቻለሁ።” ቅርጫቱንም በአምላክህ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ፊት አስቀምጠው፤ በአምላክህ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ፊት ስገድ።

11 ከዚያም አንተ፣ ሌዋዊውና በመካከልህ የሚኖረው መጻተኛ፣ አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ለአንተና ለቤትህ በሰጠው በጎ ነገር ሁሉ ደስ ይበላችሁ።

12 የዐሥራት ዓመት የሆነውን የሦስተኛውን ዓመት ምርት አንድ ዐሥረኛ ለይተህ ካወጣህ በኋላ በየከተሞችህ ውስጥ በልተው እንዲጠግቡ፣ ለሌዋዊው፣ ለመጻተኛው፣ አባት ለሌለውና ለመበለቲቱ ስጣቸው፤

13 ከዚያ በኋላ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) እንዲህ በል፤ “በሰጠኸኝ ትእዛዝ መሠረት የተቀደሰውን ክፍል ከቤቴ አውጥቼ ለሌዋዊው፣ ለመጻተኛው፣ አባት ለሌለውና ለመበለቲቱ ሰጥቻለሁ። ከትእዛዝህ አልወጣሁም፤ አንዱንም አልረሳሁም።

14 በሐዘን ላይ ሳለሁ፣ ከተቀደሰው ክፍል ላይ ምንም አልበላሁም፤ ባልነጻሁበትም ጊዜ ከዚሁ ላይ ያነሣሁትም ሆነ ለሙታን ያቀረብሁት ምንም ነገር የለም፤ አምላኬን እግዚአብሔርን (ኤሎሂም ያህዌ) ታዝዣለሁ፤ ያዘዝኸኝንም ሁሉ ፈጽሜአለሁ።