ዘዳግም 33 NASV

ሙሴ የእስራኤልን ነገዶች ባረከ

1 የእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰው ሙሴ ከመሞቱ በፊት ለእስራኤላውያን የሰጠው ቃለ ቡራኬ ይህ ነው፤

2 እንዲህም አለ፦“እግዚአብሔር (ያህዌ) ከሲና መጣ፤በእነርሱም ላይ ከሴይር እንደ ማለዳ ፀሓይ ወጣ፤ከፋራን ተራራ አበራላቸው፤ከአእላፋት ቅዱሳኑ ጋር መጣ፤በስተ ቀኙ የሚነድ እሳት ነበር።

3 በእርግጥ ሕዝቡን የምትወድ አንተ ነህ፤ቅዱሳኑ ሁሉ በእጅህ ውስጥ ናቸው።ከእግርህ ሥር ሁሉ ይሰግዳሉ፤ከአንተ ትእዛዝ ይቀበላሉ፤

4 ይህ ሙሴ የሰጠን ሕግ፣የያዕቆብ ጉባኤ ርስት ነው።

5 የሕዝቡ አለቆች ከእስራኤል ነገዶች ጋር ሆነው፣በአንድነት በተሰበሰቡ ጊዜ፣እርሱ በይሹሩን ላይ ንጉሥ ነበር።

6 “ሮቤል በሕይወት ይኑር፤ አይሙት፤የወገኖቹ ቊጥርም አይጒደልበት።”

7 ስለ ይሁዳ የተናገረው ይህ ነው፦“እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ የይሁዳን ጩኸት ስማ፤ወደ ወገኖቹም አምጣው።በገዛ እጆቹ ራሱን ይከላከላል፤አቤቱ ከጠላቶቹ ጋር ሲዋጋ ረዳቱ ሁን!

8 ስለ ሌዊም እንዲህ አለ፦“ቱሚምህና ኡሪምህ፣ለምትወደው ሰው ይሁን፤ማሳህ በተባለው ቦታ ፈተንኸው፤በመሪባም ውሃ ከእርሱ ጋር ተከራከርህ።

9 ስለ አባቱና ስለ እናቱ ሲናገርም፣‘ስለ እነርሱ ግድ የለኝም’ አለ።ወንድሞቹን አልለያቸውም፤ልጆቹንም አላወቃቸውም።ለቃልህ ማን ጥንቃቄ አደረገ፤ኪዳንህንም ጠበቀ።

10 ሥርዐትህን ለያዕቆብ፣ሕግህንም ለእስራኤል ያስተምራል።ዕጣን በፊትህ፣የሚቃጠለውን መሥዋዕት ሁሉ በመሠዊያህ ላይ ያቀርባል።

11 እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ ኀይሉን ሁሉ ባርክለት፤በእጁ ሥራ ደስ ይበልህ፤በእርሱ ላይ የሚነሡበትን ሽንጣቸውን ቊረጠው፤ጠላቶቹንም እንዳያንሠራሩ አድርገህ ምታቸው።”

12 ስለ ብንያም እንዲህ አለ፦“የእግዚአብሔር (ያህዌ) ወዳጅ የሆነ በእርሱ ተጠብቆ በሰላም ይረፍ፤ቀኑን ሙሉ ይጋርደዋልና፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) የሚወደውም ሰው በትከሻዎቹ መካከል ያርፋል።”

13 ስለ ዮሴፍ ደግሞ እንዲህ አለው፦“እግዚአብሔር (ያህዌ) ምድሩን ይባርክ፤ድንቅ የሆነውን ጠል ከላይ ከሰማይ በማውረድ፣ከታች የተንጣለለውን ጥልቅ ውሃ በመስጠት፤

14 ፀሓይ በምታስገኘው ምርጥ ፍሬ፣ጨረቃም በምትሰጠው እጅግ መልካም ነገር፤

15 ከጥንት ተራሮች በተገኘ ምርጥ ስጦታ፣በዘላለማዊ ኰረብቶች ፍሬያማነት፤

16 ምድር በምታስገኘው ምርጥ ስጦታና በሙላቷ፣በሚቃጠለው ቊጥቋጦም ውስጥ በነበረው በእርሱ ሞገስ።እነዚህ ሁሉ በወንድሞቹ መካከል ገዥ በሆነው፣በዮሴፍ ዐናት ላይ ይውረዱ።

17 በግርማው እንደ በኵር ኰርማ ነው፤ቀንዶቹም የጐሽ ቀንዶች ናቸው።በእነርሱም ሕዝቦችን፣በምድር ዳርቻ ላይ ያሉትን እንኳ ሳይቀር ይወጋል፤እነርሱም የኤፍሬም ዐሥር ሺዎቹ ናቸው፤የምናሴም ሺዎቹ እንደዚሁ ናቸው።”

18 ስለ ዛብሎንም እንዲህ አለ፦“ዛብሎን ሆይ፤ ወደ ውጭ በመውጣትህ፣አንተም ይሳኮር በድንኳኖችህ ውስጥ ደስ ይበልህ፤

19 አሕዛብን ወደ ተራራው ይጠራሉ፤በዚያም የጽድቅን መሥዋዕት ያቀርባሉ።በባሕሮች ውስጥ ያለውን በተትረፈረፈ ብልጽግና፣በአሸዋውም ውስጥ የተደበቀውን ሀብት ይደሰቱበታል።”

20 ስለ ጋድም እንዲህ አለ፦“የጋድን ግዛት የሚያሰፋ የተመሰገነ ነው!ክንድንና ራስን በመገነጣጠል፣ጋድ እንደ አንበሳ በዚያ ይኖራል።

21 ለም የሆነውን መሬት ለራሱ መረጠ፤የአለቃም ድርሻ ለእርሱ ተጠብቆለታል።የሕዝቡ መሪዎች በተሰበሰቡ ጊዜ፣ የእግዚአብሔርን (ያህዌ) የቅን ፈቃድና፣በእስራኤል ላይ የበየነውን ፍርዱን ፈጸመ።”

22 ስለ ዳንም እንዲህ አለ፦“ዳን ከባሳን ዘሎ የሚወጣ፣የአንበሳ ደቦል ነው።”

23 ስለ ንፍታሌምም እንዲህ አለ፦“ንፍታሌም በእግዚአብሔር (ያህዌ) ሞገስ ረክቶአል፤በበረከቱም ተሞልቶአል፤ባሕሩንና የደቡብን ምድር ይወርሳል።”

24 ስለ አሴርም እንዲህ አለ፦“አሴር ከሌሎች ልጆች ይልቅ የተባረከ ነው፤በወንድሞቹ ዘንድ ተወዳጅ ይሁን፤እግሩንም በዘይት ውስጥ ያጥልቅ።

25 የደጃፍህ መቀርቀሪያ ብረትና ናስ ይሆናል፤ኀይልህም በዘመንህ ሁሉ ይኖራል።

26 አንተን ለመርዳት በሰማያት ላይ፣በግርማው በደመናትም የሚገሠግሥ፣እንደ ይሽሩን አምላክ (ኤሎሂም) ያለ ማንም የለም።

27 ዘላለማዊ አምላክ (ኤሎሂም) መኖርያህ ነው፤የዘላለም ክንዶቹም ከሥርህ ናቸው፤‘እርሱን አጥፋው!’ በማለት፣ጠላትህን ከፊትህ ያስወግደዋል።

28 ስለዚህ እስራኤል ብቻውን በሰላም ይኖራል፤የሰማያት ጠል በሚወርድበት፣እህልና የወይን ጠጅ ባለበት ምድር፣የያዕቆብ ምንጭ የሚነካው የለም።

29 እስራኤል ሆይ፤ አንተ ቡሩክ ነህ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) ያዳነው ሕዝብ፣እንዳንተ ያለ ማን አለ?እርሱ ጋሻህና ረዳትህ፣ የክብርህም ሰይፍ ነው።ጠላቶችህ በፍርሀት ከፊትህ ያፈገፍጋሉ፤አንተም የማምለኪያ ኰረብታቸውንመረማመጃ ታደርጋለህ።

ምዕራፎች

1 2 3 4 5 6 7 8 9 10 11 12 13 14 15 16 17 18 19 20 21 22 23 24 25 26 27 28 29 30 31 32 33 34