ዘዳግም 7:3-9 NASV

3 ከእነርሱ ጋር ጋብቻ አታድርግ፤ ሴት ልጆችህን ለወንድ ልጆቻቸው አትስጥ፤ ወይም ለወንድ ልጆችህ ሴት ልጆቻቸውን አታምጣ፤

4 ምክንያቱም እኔን ከመከተል ልጆችህን መልሰው ሌሎችን አማልክት እንዲያመልኩ ስለሚያደርጉና ከዚህም የተነሣ የእግዚአብሔር (ያህዌ) ቊጣ በላይህ ነዶ፣ ፈጥኖ ስለሚያጠፋህ ነው።

5 እንግዲህ በእነርሱ ላይ የምታደርጉት ይህ ነው፤ መሠዊያዎቻቸውን አፈራርሱ፤ የማምለኪያ ዐምዶቻቸውን ሰባብሩ፤ የአሼራ ምስል ዐምዶቻቸውን ቊረጡ፤ ጣዖቶቻቸውንም በእሳት አቃጥሉ።

6 አንተ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ቅዱስ ሕዝብ ስለ ሆንህ፣ አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) የራሱ ሕዝብ፣ ርስትም እንድትሆንለት በምድር ላይ ከሚኖሩ ሕዝቦች ሁሉ መረጠህ።

7 እግዚአብሔር (ያህዌ) እናንተን የወደዳችሁና የመረጣችሁ ከሌሎች ሕዝቦች በቊጥር ስለ በዛችሁ አይደለም፤ ቊጥራችሁማ ከሕዝቦች ሁሉ እጅግ አነስተኛ ነበር።

8 ነገር ግን እናንተን በብርቱ እጅ ያወጣችሁ፣ ከባርነት ምድርና ከግብፅ ንጉሥ ከፈርዖን መዳፍ የተቤዣችሁ፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) እናንተን ስለወደዳችሁና ለአባቶቻችሁ የማለላቸውን መሐላ ስለ ጠበቀ ነው።

9 ስለዚህም አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) አምላክ (ኤሎሂም) መሆኑን ዕወቅ፤ እርሱ ለሚወዱትና ትእዛዞቹን ለሚጠብቁት የፍቅሩን ኪዳን እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ የሚጠብቅ ታማኝ አምላክ (ኤሎሂም) ነው።