2 ዜና መዋዕል 25:15-21 NASV

15 የእግዚአብሔርም ቊጣ በአሜስያስ ላይ ነደደ፤ ነቢይንም ላከበት፤ ነቢዩም፣ “የገዛ ሕዝባቸውን ከእጅህ ማዳን ያልቻሉትን የአሕዛብን አማልክት ርዳታ የጠየቅኸው ለምንድን ነው?” አለው።

16 እርሱም በመናገር ላይ ሳለ፣ ንጉሡ፣ “ለመሆኑ አንተን የንጉሥ አማካሪ አድርገን ሾመነሃልን? ዝም አትልም እንዴ! መሞት ትፈልጋለህ?” አለው።ነቢዩም ዝም አለ፤ ሆኖም፣ “ይህን አድርገሃልና ምክሬንም አልሰማህምና፤ እግዚአብሔር ሊያጠፋህ እንደወሰነ ዐውቃለሁ” አለ።

17 የይሁዳ ንጉሥ አሜስያስ አማካሪዎቹን ካማከረ በኋላ፣ የእስራኤል ንጉሥ የኢዩ የልጅ ልጅ፣ የኢዮአካዝ ልጅ ወደ ሆነው ወደ ኢዮአስ፣ “እስቲ ናና ፊት ለፊት እንጋጠም” ሲል ላከበት።

18 የእስራኤል ንጉሥ ኢዮአስ ግን፣ ለይሁዳ ንጉሥ ለአሜስያስ እንዲህ ሲል መለሰለት፤ “አንድ የሊባኖስ ኵርንችት፣ ‘ሚስት እንድትሆነው ሴት ልጅህን ለልጄ ስጠው’ ሲል ወደ ሊባኖስ ዝግባ ላከበት። ከዚያም የዱር አውሬ ከሊባኖስ ወጥቶ ኵርንችቱን ረገጠው።

19 ኤዶምን አሸንፌአለሁ ብለህ ራስህን በትዕቢት ክበኸዋል፤ ኮርተሃልም፤ ግን ዐርፈህ እቤትህ ተቀመጥ! በራስህና በይሁዳ ላይ ውድቀት ታመጣ ዘንድ ችግር የምትጠራው ስለምንድን ነው?”

20 የኤዶምን አማልክት ማምለክ በመፈለጋቸው፣ እግዚአብሔር በጠላቶቻቸው እጅ አሳልፎ ሊሰጣቸው ወስኖአልና፣ አሜስያስ አላዳመጣቸውም።

21 ስለዚህ የእስራኤል ንጉሥ ኢዮአስ አደጋ ጣለ። እርሱና የይሁዳ ንጉሥ አሜስያስ በይሁዳ ውስጥ ቤትሳሚስ በተባለ ስፍራ ፊት ለፊት ተጋጠሙ።