2 ዜና መዋዕል 8:13-18 NASV

13 ሙሴ ስለ መሥዋዕት አቀራረብ ባዘዘው መሠረት በእያንዳንዱ የበዓል ቀን ይኸውም በየሰንበቱ፣ በየወሩ መባቻና በሦስቱ የዓመት በዓላት ማለትም በቂጣ በዓል፣ በመከር በዓልና በዳስ በዓል ጊዜ የሚቃጠለውን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር አቀረበ።

14 የአባቱን የዳዊትን ሥርዐት በመከተልም፣ ካህናቱን በየአገልግሎት ክፍላቸው ሌዋውያኑንም ምስጋናውን እንዲመሩና በየዕለቱ ሥራቸው ካህናቱን እንዲረዱ መደባቸው። ደግሞም የእግዚአብሔር ሰው ዳዊት ባዘዘው መሠረት የቤተ መቅደሱን በር ጠባቂዎች በልዩ ልዩ በሮች ጥበቃ ላይ በየክፍላቸው መደባቸው።

15 እነርሱም ንጉሡ ግምጃ ቤቱን ጨምሮ ስለማናቸውም ነገር ለካህናቱና ለሌዋውያኑ የሰጠውን ትእዛዝ አልተላለፉም ነበር።

16 የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሠረት ከተጣለበት ዕለት አንሥቶ እስከ ፍጻሜው ድረስ ያለው የሰሎሞን ሥራ ሁሉ ተከናወነለት፤ በዚሁ ሁኔታም የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ሥራ ከፍጻሜ ደረሰ።

17 ከዚያም ሰሎሞን የኤዶም የባሕር ጠረፍ ወደሆኑት ወደ ዔዮንጋብርና ወደ ኤሎት ሄደ።

18 ኪራምም ባሕሩን በሚያውቁት በራሱ መኮንኖች የሚታዘዙ መርከቦችን ላከለት፤ እነዚህም ከሰሎሞን ሰዎች ጋር በመሆን ወደ ኦፊር ተጓዙ፤ ከዚያም አራት መቶ አምሳ መክሊት ወርቅ አምጥተው ለንጉሥ ሰሎሞን ሰጡት።