2 ዜና መዋዕል 8:5-11 NASV

5 እንዲሁም የላይኛውን ቤት ሖሮንና የታችኛውን ቤትሖሮን የተመሸጉ ከተሞች አድርጎ ከቅጥሮቻቸው፣ ከበሮቻቸውና ከመዝጊያዎቻቸው ጋር ሠራ።

6 ደግሞም ባዕላትንና የዕቃ ቤት ከተሞቹን ሁሉ፣ ሠረገሎችና ፈረሶች የሚኖሩባቸውን ከተሞች ሁሉ፣ ባጠቃላይ በኢየሩሳሌም፣ በሊባኖስና በግዛቱ ሁሉ ለመሥራት የፈለጋቸውን ነገሮች ሁሉ ሠራ።

7 እስራኤላውያን ያልሆኑ ግን ከኬጢያውያን፣ ከአሞራውያን፣ ከፌርዜያውያን፣ ከኤዊያውያንና ከኢያቡሳውያን የቀሩት ሕዝቦች ሁሉ፣

8 እስራኤላውያን ያላጠፏቸውን፣ በምድሪቱ የቀሩ ዘሮቻቸውን የጒልበት ሥራ ይሠሩ ዘንድ ሰሎሞን መለመላቸው፤ እስከ ዛሬም ይሠራሉ።

9 ይሁን እንጂ ሰሎሞን ማንም እስራኤላዊ ባሪያ ሆኖ በግዳጅ ሥራውን እንዲሠራ አላደረገም፤ እነርሱ ተዋጊዎች፣ የሻምበል አዛዦች፣ የሠረገሎችና የሠረገላ ነጂዎች አዛዦች ነበሩና።

10 ከእነዚህም ሁለት መቶ አምሳዎቹ የንጉሥ ሰሎሞን ሹማምት ሰዎቹን የሚቈጣጠሩ ነበሩ።

11 ሰሎሞንም፣ “የእግዚአብሔር ታቦት የገባበት ቦታ ሁሉ ቅዱስ ስለ ሆነ፣ ሚስቴ በእስራኤል ንጉሥ በዳዊት ቤተ መንግሥት መኖር አይገባትም” በማለት የፈርዖንን ልጅ ከዳዊት ከተማ እርሱ ወደሠራላት ቤተ መንግሥት አመጣት።