2 ዜና መዋዕል 23:8-14 NASV

8 ሌዋውያኑና ይሁዳ ሁሉ ልክ ካህኑ ዮዳሄ እንዳዘዘው አደረጉ፤ ካህኑ ዮዳሄ ከጥበቃ ክፍሎች የትኛውንም አላሰናበተም ነበርና፣ እያንዳንዱ በሰንበት ቀን በሥራ ላይ የሚሰማሩትንና ከሥራ የሚወጡትን የራሱን ሰዎች ወሰደ፤

9 ከዚያም በቤተ መቅደሱ የነበሩትን የንጉሥ ዳዊት ጦሮች፣ ታላላቅና ታናናሽ ጋሻዎች ለመቶ አለቆቹ ሰጣቸው።

10 ሰዎቹም ሁሉ እያንዳንዳቸው መሣሪያቸውን በእጃቸው እንደ ያዙ ከቤተ መቅደሱ ደቡብ አንሥቶ እስከ ሰሜን ድረስ በመሠዊያውና በቤተ መቅደሱ አጠገብ በንጉሡ ዙሪያ እንዲቆሙ አደረገ።

11 ዮዳሄና ወንዶች ልጆቹ የንጉሡን ልጅ አምጥተው ዘውድ ጫኑለት፤ የኪዳኑንም መጽሐፍ ሰጥተውት አነገሡት፤ ቀብተውትም፣ “ንጉሡ ለዘላለም ይኑር!” እያሉ ጮኹ።

12 ጎቶልያም የሚሯሯጠውንና ደስታውን ለንጉሡ የሚገልጠውን ሕዝብ ሁካታ ስትሰማ፣ ሕዝቡ ወዳለበት ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ሄደች።

13 ንጉሡ በመግቢያው ላይ ባለው በዐምዱ አጠገብ ቆሞ አየች፣ የጦር መኮንኖችና መለከት ነፊዎችም በንጉሡ አጠገቡ ነበሩ፤ የምድሪቱ ሕዝብ ሁሉ ይደሰቱ፣ መለከትም ይነፉ ነበር፤ መዘምራንም በዜማ ዕቃ ታጅበው የበዓሉን ዝማሬ ይመሩ ነበር፤ ጎቶልያም ልብሷን ቀድዳ፣ ይህ ዐመፅ ነው! ይህ ዐመፅ ነው!” ብላ ጮኸች።

14 ካህኑ ዮዳሄም የወታደር አዛዥ ወደሆኑት ወደ መቶ አለቆቹ፣ “በሰልፉ መካከል አውጥታችሁ አምጧት፤ የሚከተላት ካለም በሰይፍ ግደሉት” ሲል ላከባቸው። ካህኑም፣ “በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አትግደሏት” ብሎ ነበርና።