2 ዜና መዋዕል 8:7-13 NASV

7 እስራኤላውያን ያልሆኑ ግን ከኬጢያውያን፣ ከአሞራውያን፣ ከፌርዜያውያን፣ ከኤዊያውያንና ከኢያቡሳውያን የቀሩት ሕዝቦች ሁሉ፣

8 እስራኤላውያን ያላጠፏቸውን፣ በምድሪቱ የቀሩ ዘሮቻቸውን የጒልበት ሥራ ይሠሩ ዘንድ ሰሎሞን መለመላቸው፤ እስከ ዛሬም ይሠራሉ።

9 ይሁን እንጂ ሰሎሞን ማንም እስራኤላዊ ባሪያ ሆኖ በግዳጅ ሥራውን እንዲሠራ አላደረገም፤ እነርሱ ተዋጊዎች፣ የሻምበል አዛዦች፣ የሠረገሎችና የሠረገላ ነጂዎች አዛዦች ነበሩና።

10 ከእነዚህም ሁለት መቶ አምሳዎቹ የንጉሥ ሰሎሞን ሹማምት ሰዎቹን የሚቈጣጠሩ ነበሩ።

11 ሰሎሞንም፣ “የእግዚአብሔር ታቦት የገባበት ቦታ ሁሉ ቅዱስ ስለ ሆነ፣ ሚስቴ በእስራኤል ንጉሥ በዳዊት ቤተ መንግሥት መኖር አይገባትም” በማለት የፈርዖንን ልጅ ከዳዊት ከተማ እርሱ ወደሠራላት ቤተ መንግሥት አመጣት።

12 ሰሎሞንም በቤተ መቅደሱ መመላለሻ ፊት ለፊት ባሠራው የእግዚአብሔር መሠዊያ ላይ የሚቃጠል መሥዋዕት ለእግዚአብሔር አቀረበ።

13 ሙሴ ስለ መሥዋዕት አቀራረብ ባዘዘው መሠረት በእያንዳንዱ የበዓል ቀን ይኸውም በየሰንበቱ፣ በየወሩ መባቻና በሦስቱ የዓመት በዓላት ማለትም በቂጣ በዓል፣ በመከር በዓልና በዳስ በዓል ጊዜ የሚቃጠለውን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር አቀረበ።