1 የእግዚአብሔር ባሪያ ሙሴ ከሞተ በኋላ፣ እግዚአብሔር የሙሴን አገልጋይ የነዌን ልጅ ኢያሱን እንዲህ አለው፤
2 “እነሆ፤ ባሪያዬ ሙሴ ሞቶአል፤ እንግዲህ አሁንም አንተና ይህ ሕዝብ ሁሉ ተነሡ፤ ለእሥራኤላውያን ወደምሰጣቸው ምድር ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻገሩ።
3 ለሙሴ በሰጠሁትም ተስፋ መሠረት፣ እግራችሁ የሚረግጠውን ቦታ ሁሉ እሰጣችኋለሁ።
4 የርስታችሁ ዳርቻ ከምድረ በዳው እስከ ሊባኖስ፣ ከታላቁ ወንዝ ከኤፍራጥስ አንሥቶ፣ የኬጢያውያንን ምድር በሙሉ ይዞ፣ በምዕራብ በኩል እስከ ታላቁ ባሕር ይደርሳል።
5 በሕይወት በምትኖርበት ዘመን ሁሉ ማንም አይቋቋምህም፤ ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ ሁሉ ከአንተም ጋር እሆናለሁ፤ ከቶ አልጥልህም፤ አልተውህም።
6 “ጽና፤ ለቀደሙት አባቶቻቸው እሰጣችኋለሁ ብዬ የማልሁላቸውን ምድር እንዲወርሱ፣ ይህን ሕዝብ የምትመራው አንተ ነህና በርታ።
7 አይዞህ፤ ብቻ አንተ በርታ፤ ባሪያዬ ሙሴ የሰጠህን ትእዛዝ ሁሉ በጥንቃቄ ጠብቅ፤ በምትሄድበትም ሁሉ እንዲሳካልህ፣ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አትበል።