ዘፀአት 29:16-22 NASV

16 አውራውንም በግ እረደው፤ ደሙንም ወስደህ በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው።

17 አውራ በጉን በየብልቱ ቈራርጠህ፣ የሆድ ዕቃውንና እግሮቹን አጥበህ ከራሱና ከሌሎቹ ቁርጥራጭ ብልቶች ጋር አኑረው።

18 ከዚያም አውራ በጉን በሙሉ በመሠዊያው ላይ አቃጥለው፤ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚቃጠል መሥዋዕት ጣፋጭ መዓዛና ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት ነው።

19 “ሌላውን አውራ በግ ወስደህ አሮንና ወንዶች ልጆቹ በራሱ ላይ እጆቻቸውን ይጭኑበታል።

20 አውራውንም በግ እረደው፤ ከደሙም ወስደህ የአሮንንና የወንዶች ልጆቹን የቀኝ ጆሮዎቻቸውን ጫፍ የቀኝ እጆቻቸውን አውራ ጣቶች፣ የቀኝ እግራቸውንም አውራ ጣቶች ቅባቸው፤ ከዚያም ደሙን በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው።

21 በመሠዊያው ላይ ካለው ደምና ከቅብዐ ዘይቱ ወስደህ በአሮንና በልብሶቹ ላይ እንዲሁም በወንዶች ልጆቹና በልብሶቻቸው ላይ እርጨው። ከዚያም እርሱና ወንዶች ልጆቹ እንዲሁም ልብሶቻቸው የተቀደሱ ይሆናሉ።

22 ‘ከዚህ አውራ በግ ስቡን፣ ላቱን፣ በሆድ ዕቃው ውስጥ ያለውን ስብ፣ የጉበቱን ሽፋን፣ ሁለቱን ኵላሊቶችና በዙሪያቸው ያለውን ስብና ቀኙን ወርች ውሰድ፤ ይህ የክህነት አውራ በግ ነው።