ሚልክያስ

ምዕራፎች 2

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ለካህናት የተሰጠ ማስጠንቀቂያ

1“አሁንም ካህናት ሆይ፤ ይህ ማስጠንቀቂያ ለእናንተ የተሰጠ ነው፤ 2ባትሰሙ፣ ልባችሁንም ስሜን ለማክበር ባታዘጋጁ፣ ርግማን እሰድባችኋለሁ፤ በረከታችሁንም ወደ መርገም እለውጠዋለሁ፤ ልታከብሩኝ ልባችሁን አላዘጋጃችሁምና’ ረግሜዋለሁ ይላል እግዚአብሔር ጸባኦት። 3“ዘራችሁን እገሥጻለሁ፤ የመሥዋታችሁን ፋንድያ በፊታችሁ ላይ እበትናለሁ፤ እናንተም ከእርሱ ጋር ትወገዳላችሁ፤ 4ከሌዊ ጋር የገባሁት ኪዳን ይጸና ዘንድ፣ ይህን ማስጠንቀቂያ የላክሁት እኔ መሆኔንም ታውቃላችሁ” ይላል እግዚአብሔር ጸባኦት። 5“ከእርሱ ጋር የገባሁት ኪዳን የሕይወትና የሰላም ኪዳን ነበር፤ እነርሱንም ሰጠሁት፤ ይህም ክብርን አመጣ፤ እርሱም አከበረኝ፤ ስሜንም በመፍራትም ጸና። 6እውነተኛ ትምህርት በአፉ ነበር፤ ምንም ዐይነት የሐሰት ነገር በአንደበቱ አልተገኘም፤ ከእኔ ጋር በሰላምና በቅንነት ተራመደ፤ ብዙዎችንም ከኀጢአት መለሰ። 7“ካህኑ የሁሉ ገዥ፣ የእግዚአብሔር መልእክተኛ ስለ ሆነ ከንፈሮቹ ዕውቀትን ሊጠብቁ፣ ሰዎችም ከአንደበቱ ትምህርትን ሊፈልጉ ይገባል፤ 8እናንተ ግን ከመንገዱ ወጥታችኋል፤ በትምህርታችሁም ብዙዎች እንዲሰናከሉ አድርጋችኋል፤ የሌዊንም ኪዳን አፍርሳችኋል” ይላል እግዚአብሔር ጸባኦት። 9“ስለዚህ በመንገዴ ስላልሄዳችሁና በትምህርታችሁም አድልዎ ስላደረጋችሁ፣ በሰዎች ሁሉ ፊት እንድትናቁና እንድትዋረዱ አድርጌአችኋለሁ።”

የይሁዳ አለመታመን

10ሁላችን አንድ አባት ያለን አይደለንምን? የፈጠረንስ አንድ አምላክ አይደለምን? ታዲያ እርስ በርሳችን ታማኝነት በማጒደል የአባቶቻችንን ኪዳን ለምን እናረክሳለን? 11ይሁዳ አልታመነም፤ በእስራኤልና በኢየሩሳሌምም አስጸያፊ ነገር ተፈጽሞአል፤ ይሁዳ የባዕድ አምላክ ሴት ልጅ በማግባት እግዚአብሔር የሚወደውን መቅደስ አርክሶአል። 12ይህን የሚያደርግ ማንኛውም ሰው ቢሆን፣ ለእግዚአብሔር ጸባኦት ቊርባን ቢያመጣም እንኳ፣ እግዚአብሔር ከያዕቆብ ድንኳን ያስወግደው። 13ሌላው የምታደርጉት ነገር ደግሞ፣ የእግዚአብሔርን መሠዊያ በእንባ ታጥለቀልቃላችሁ፤ ከእንግዲህ ወዲያ ቊርባናችሁን ስለ ማይመለከትና በደስታም ከእጃችሁ ስለማይቀበል ታለቅሳላችሁ፤ ትጮኻ ላችሁም። 14እናንተም፣ “ለምን ይህ ሆነ?” ብላችሁ ትጠይቃላችሁ። ይህ የሆነው የትዳር ጓደኛህን፣ አጋርህንና የቃል ኪዳን ሚስትህን፣ አታለሃታልና እግዚአብሔር በአንተና በወጣትነት ሚስትህ መካከል ላለው ቃል ኪዳን ምስክር ስለ ሆነ ነው። 15 እግዚአብሔር አንድ አላደረጋቸውምን? በሥጋም በመንፈስም የእርሱ ናቸው። ለምን አንድ አደረጋቸው? ፈሪሀ እግዚአብሔር ያለውን ዘር ይፈልግ ስለ ነበር ነው። ስለዚህ በመንፈሳችሁ ራሳችሁን ጠብቁ፤ ከወጣትነት ሚስታችሁም ጋር ያላችሁን ታማኝነት አታጓድሉ። 16“ፍችን እጠላለሁ” ይላል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር፤ ልብሱን በግፍ ድርጊት የሚሸፍነውንም ሰው እጠላለሁ” ይላል እግዚአብሔር ጸባኦት።ስለዚህ በመንፈሳችሁ ራሳችሁን ጠብቁ፤ ታማኝነታችሁም አይጓደል።

የፍርድ ቀን

17 እግዚአብሔርን በቃላችሁ አታክታችሁታል።እናንተም፣ “ያታከትነው እንዴት ነው?” ትላላችሁ?“ክፉ የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መልካም ነው፤ እርሱም በክፉዎች ደስ ይለዋል” ወይም “የፍትሕ አምላክ ወዴት ነው?” በማለታችሁ ነው።

ምዕራፎች