20 ክፉ ሰው ዕድሜውን ሙሉ፣ጨካኙም በተመደበለት ዘመን ሁሉ ይሠቃያል።
21 የሚያስደነግጥ ድምፅ በጆሮው ላይ ይጮኻል፤በሰላም ጊዜ ቀማኞች አደጋ ያደርሱበታል።
22 ከጨለማ ወጥቶ ማምለጥ ይፈራል፤ለሰይፍም የተመደበ ነው።
23 የአሞራ እራት ለመሆን ይቅበዘበዛል፤የጨለማ ቀን መቅረቡን ያውቃል።
24 ጭንቀትና ሐዘን ያስፈራሩታል፤ለማጥቃት እንደ ተዘጋጀ ንጉሥም ያይሉበታል፤
25 እጁን በእግዚአብሔር ላይ አንሥቶአልና፤ሁሉን የሚችለውን አምላክም ደፍሮአል፤
26 ወፍራምና ጠንካራ ጋሻ አንግቦ፣ሊቋቋመው ወጥቶአል።