ኢዮብ

ምዕራፎች 32

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ኤሊሁ

1ኢዮብ በበኩሉ ራሱን እንደ ጻድቅ ቈጥሮ ስለ ነበር፣ እነዚህ ሦስት ሰዎች ለእርሱ መልስ መስጠታቸውን ተዉ። 2ከራም ወገን የሆነው፣ የቡዛዊው የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ ግን ኢዮብ ከእግዚአብሔር ይልቅ ራሱን ጻድቅ ስላደረገ፣ እጅግ ተቈጣው። 3ሦስቱ የኢዮብ ጓደኞች በኢዮብ ላይ መፍረድ እንጂ፣ ነገሩን ሊያሳምኑት ስላልቻሉ፣ በእነርሱም ላይ ተቈጣ። 4ኤሊሁ፣ ሌሎቹ በዕድሜ ይበልጡት ስለ ነበር ከእነርሱ ቀድሞ ለኢዮብ ሳይናገር ቈየ። 5ነገር ግን እነዚህ ሦስቱ የሚሉትን ባጡ ጊዜ ቍጣው ነደደ። 6ስለዚህ የቡዛዊው የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ እንዲህ አለ፤“እኔ በዕድሜ ታናሽ ነኝ፤እናንተ ግን አዛውንቶች ናችሁ፤ከዚህም የተነሣ የማውቀውን ለመናገር አልደፈርሁም፤ፈርቼ ዝም አልሁ። 7‘ዕድሜ ይናገራል፤ረጅም ዘመን ጥበብን ያስተምራል’ ብዬ ነበር። 8ነገር ግን በሰው ያለው መንፈስ፣ሁሉን የሚችል አምላክ እስትንፋስ፣ማስተዋልን ይሰጣል። 9ጠቢባን የሚሆኑት በዕድሜ የገፉ ብቻ አይደሉም፤የሚያስተውሉም ሽማግሌዎች ብቻ አይደሉም። 10“ስለዚህ፣ ‘ስሙኝ፣እኔም የማውቀውን ልንገራችሁ’ እላለሁ። 11እናንተ በምትነጋገሩበት ጊዜ ታገሥሁ፤ቃላት እየመረጣችሁ ስትናገሩ፣በጥሞና ሰማኋችሁ፤ 12በሙሉ ልብ አዳመጥኋችሁ፤ነገር ግን ከእናንተ የኢዮብን ቃል ያስተባበለ ማንም የለም፤ለንግግሩም አጸፋ የመለሰ አልተገኘም። 13‘እኛ ጥበብ አግኝተናል፤ሰው ሳይሆን እግዚአብሔር ይርታው’ አትበሉ። 14ኢዮብ ግን ቃሉን በእኔ ላይ አልሰነዘረም፤እኔም እንደ እናንተ አነጋገር መልስ አልሰጠውም። 15“እነርሱ ተስፋ ቈርጠው፤ የሚሉት የላቸውም፤የሚናገሩትም ጠፍቶአቸዋል። 16እንግዲህ እነርሱ መልስ ስላጡ፣ጸጥ ብለውም ስለ ቆሙ፣ በትዕግሥት ልጠብቅን? 17እኔም የምለው ይኖረኛል፤የማውቀውንም እገልጣለሁ። 18የምናገረው ሞልቶኛልና፤በውስጤ ያለውም መንፈስ ገፋፍቶኛል። 19ውስጤ እንደ ተከደነና መተንፈሻ እንዳጣ የወይን ጠጅ፣ሊፈነዳ እንደ ተቃረበም አዲስ የወይን ጠጅ አቁማዳ ሆኖአል። 20ተናግሬ መተንፈስ አለብኝ፤አፌንም ከፍቼ መልስ መስጠት ይገባኛል። 21ለማንም አላደላም፤ሰውንም አላቈላምጥም።