24 አገልጋዬ ካሌብ ግን የተለየ መንፈስ ስላለውና በፍጹም ልቡ የተከተለኝ በመሆኑ ሄዶባት ወደ ነበረችው ምድር አስገባዋለሁ፤ ዘሮቹም ይወርሷታል።
25 አማሌቃውያንና ከነዓናውያን በሸለቆው የሚኖሩ ስለ ሆነ በነገው ዕለት ተመልሳችሁ በቀይ ባሕር መንገድ ወደ ምድረ በዳው ሂዱ።”
26 እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፤
27 “ይህ ክፉ ማኅበረሰብ በእኔ ላይ የሚያጒረመርመው እስከ መቼ ነው? የእነዚህን ነጭናጮች እስራኤላውያን ማጒረምረም ሰምቻለሁ።
28 ስለዚህ እንዲህ በላቸው፤ ‘እግዚአብሔር (ያህዌ) እንዲህ ይላል፤ እኔ ሕያው ነኝ፤ ስትናገሩ የሰማኋችሁን እነዚያን ነገሮች አደርግባችኋለሁ፤
29 በተደረገው ቈጠራ መሠረት፣ ሃያ ዓመት ወይም ከዚያ በላይ የሆናችሁና በእኔም ላይ ያጒረመረማችሁ ሁሉ በድናችሁ በዚህ ምድረ በዳ ይወድቃል።
30 መኖሪያችሁ እንድትሆን በጽኑ ወደ ማልሁላችሁ ምድር ከዮፎኒ ልጅ ከካሌብና ከነዌ ልጅ ከኢያሱ በስተቀር ከእናንተ አንዳችሁም አትገቡባትም።