ዘኁልቍ

ምዕራፎች 20

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ከዐለት የፈለቀ ውሃ

1በመጀመሪያው ወር መላው የእስራኤል ማኅበረሰብ ወደ ጺን ምድረ በዳ መጥተው በቃዴስ ተቀመጡ፤ እዚያ ማርያም ሞተች፤ ተቀበረችም። 2በዚህ ጊዜ ለማኅበረ ሰቡ የሚሆን ውሃ አልነበረም፤ ሕዝቡም ሙሴንና አሮንን በመቃወም ተሰበሰቡ። 3ሙሴን ተጣሉት፤ እንዲህም አሉት፤ “ወንድሞቻችን በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በሞቱ ጊዜ ምነው እኛም ያኔ ሞተን ባረፍነው ኖሮ! 4የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ማኅበረሰብ ወደዚህ ምድረ በዳ ያመጣችሁት ለምንድ ነው! ከነከብቶቻችን እዚሁ እንድናልቅ ነውን? 5ከግብፅ አውጥታችሁ እህል ወይም በለስ፣ ወይን ወይም ሮማን ወደሌለበት ወደዚህ ክፉ ቦታ ያመጣችሁንስ ለምንድ ነው? የሚጠጣ ውሃ እንኳ ይታጣ!” 6ሙሴና አሮን ከማኅበረ ሰቡ ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ሄደው በግንባራቸው ተደፉ፤ የእግዚአብሔርም (ያህዌ) ክብር ተገለጠላቸው። 7እግዚአብሔርም (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤ 8“በትሪቱን ውሰድ፤ አንተና ወንድምህ አሮን ማኅበሩን በአንድነት ሰብሰቡ፤ እነርሱም እያዩ ዐለቱን ተናገሩት፤ ዐለቱም ውሃ ያወጣል። አንተም ለማኅበረ ሰቡ ከዐለቱ ውሃ ታወጣላቸዋለህ፤ እነርሱና ከብቶቻቸውም ይጠጣሉ።” 9ስለዚህም ሙሴ ልክ እንደታዘዘው በትሩን ከእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወሰደ። 10እርሱና አሮንም ማኅበሩን በዐለቱ ፊት አንድ ላይ ሰበሰቡ፤ ሙሴም፣ “እናንት ዐመፀኞች አድምጡ፤ ከዚህ ዐለት እኛ ለእናንተ ውሃ ማውጣት አለብን?” አላቸው። 11ከዚያም ሙሴ እጁን ዘርግቶ በበትሩ ዐለቱን ሁለት ጊዜ መታው፤ ውሃውም ተንዶለዶለ፤ ማኅበረ ሰቡና ከብቶቻቸውም ጠጡ። 12ነገር ግን እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴንና አሮንን፣ “በእስራኤላውያን ፊት እኔን ቅዱስ አድርጋችሁ ለማክበር ስላልታመናችሁብኝ ይህን ማኅበረሰብ ወደምሰጠው ምድር ይዛችሁ አትገቡም” አላቸው። 13እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር (ያህዌ) ጋር የተጣሉበት፣ እርሱም ቅዱስ መሆኑን በመካከላቸው የገለጠበት ይህ የመሪባ ውሃ ነበር።

ኤዶም እስራኤል እንዳያልፍ ከለከለ

14ሙሴ ከቃዴስ ለኤዶም ንጉሥ እንዲህ ሲል መልእክተኞች ላከ፤“ወንድምህ እስራኤል የሚለው ይህ ነው፤ የደረሰብን መከራ ሁሉ ምን እንደሆነ አንተም ታውቃለህ። 15የቀድሞ አባቶቻችን ወደ ግብፅ ወረዱ፤ እኛም እዚያ ብዙ ዘመን ኖርን። ግብፃውያን እኛንም አባቶቻችንንም አሠቃዩን፤ 16ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) በጮኽን ጊዜ ግን ጩኸታችንን ሰማ፤ መልአክ ልኮም ከግብፅ አወጣን።“አሁንም ያለነው እዚሁ ቃዴስ በግዛትህ ድንበር ላይ ባለችው ከተማ ነው። 17ስለዚህ በአገርህ እንድናልፍ እባክህን ፍቀድልን፤ በየትኛውም ዕርሻ ወይም የወይን ተክል ውስጥ አንገባም፤ ከየትኛውም ጒድጓድ ውሃ አንጠጣም። የንጉሡን አውራ ጐዳና ይዘን ከመጓዝ በስተቀር፣ ግዛትህን አልፈን እስክንሄድ ድረስ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አንልም።” 18ኤዶም ግን እንዲህ ሲል መለሰ፤“በዚህ በኩል አታልፉም፤ እናልፋለን የምትሉ ከሆነ በሰልፍ ወጥተን በሰይፍ እንመታችኋለን።” 19እስራኤላውያንም መልሰው፣“አውራውን መንገድ ይዘን እንሄዳለን፤ እኛም ሆንን ከብቶቻችን የትኛውንም ውሃችሁን ከጠጣን ዋጋውን እንከፍላለን፤ በእግር አልፈን መሄድ ብቻ እንጂ ሌላ ምንም አንፈልግም።” አሏቸው። 20ኤዶምም እንደ ገና፣“በዚህ ማለፍ አትችሉም።” የሚል መልስ ሰጣቸው።ከዚያም ኤዶም ብዙና ኀይለኛ የሆነ ሰራዊት አሰልፎ ሊወጋቸው ወጣ፤ 21ስለዚህ ኤዶም በግዛቱ አልፈው እንዳይሄዱ ስለ ከለከላቸው እስራኤላውያን ተመለሱ።

የአሮን መሞት

22መላው የእስራኤል ማኅበረሰብ ከቃዴስ ተነሥቶ ወደ ሖር ተራራ መጣ። 23እግዚአብሔርም (ያህዌ) በኤዶም ወሰን አጠገብ ባለው በሖር ተራራ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፤ 24“አሮን ወደ ወገኖቹ ይሰበሰባል፤ ሁለታችሁም በመሪባ ውሃ በትእዛዜ ላይ ዐምፃችኋልና ለእስራኤላውያን ወደምሰጣት ምድር አይገባም። 25አሮንንና ልጁን አልዓዛርን ወደ ሖር ተራራ ይዘሃቸው ውጣ። 26አሮን ወደ ወገኖቹ ስለሚሰበሰብ ልብሱን አውልቀህ ልጁን አልዓዛርን አልብሰው፤ አሮንም እዚያው ይሞታል።” 27ሙሴ እግዚአብሔር (ያህዌ) እንዳዘዘው አደረገ፤ መላው ማኅበረሰብ እያያቸው ወደ ሖር ተራራ ወጡ። 28ሙሴም የአሮንን ልብስ አውልቆ ልጁን አልዓዛርን አለበሰው፤ አሮንም እዚያው ተራራው ጫፍ ላይ ሞተ። ከዚያም ሙሴና አልዓዛር ከተራራው ወረዱ፤ 29መላው ማኅበረ ሰብም አሮን መሞቱን በተረዳ ጊዜ፣ የእስራኤል ቤት በሙሉ ሠላሳ ቀን አለቀሰለት።