1 ነገሥት 5 NASV

ቤተ መቅደሱን ለመሥራት የተደረገ ዝግጅት

1 የጢሮስ ንጉሥ ኪራም በዘመኑ ሁሉ ለዳዊት ወዳጅ ስለ ነበር፣ ሰሎሞን በአባቱ እግር ለመተካት መቀባቱን በሰማ ጊዜ፣ መልእክተኞቹን ወደ ሰሎሞን ላከ።

2 ሰሎሞንም እንዲህ የሚል መልእክት ወደ ኪራም መልሶ ላከ፤

3 “አባቴ ዳዊት በዙሪያው ሁሉ ከገጠመው ጦርነት የተነሣ፣ እግዚአብሔር ጠላቶቹን ከእግሩ በታች እስኪጥልለት ድረስ ለአምላኩ ለእግዚአብሔር ስም ቤተ መቅደስ መሥራት እንዳልቻለ ታውቃለህ።

4 አሁን ግን አምላኬ እግዚአብሔር በዙሪያዬ ሁሉ ሰላም ሰጥቶኛል፤ ጠላትም የለብኝም።

5 እነሆ፣ እግዚአብሔር ለአባቴ ለዳዊት፣ ‘ለስሜ ቤተ መቅደስ የሚሠራልኝ ከአንተ ቀጥሎ በዙፋንህ የማስቀምጠው ልጅህ ነው’ ብሎ እንደ ነገረው፣ ለአምላኬ ለእግዚአብሔር ስም ቤተ መቅደስ ለመሥራት አስቤአለሁ።

6 “ስለዚህ የሊባኖስ ዝግባ እንዲቈረጥልኝ ትእዛዝ ስጥ፤ ሰዎቼ ከሰዎችህ ጋር አብረው ይሠራሉ፤ የሰዎችህንም ደመወዝ አንተ በወሰንኸው እከፍልሃለሁ፤ ከሰዎቼ መካከል እንደ ሲዶናውያን ዕንጨት በመቊረጥ እስከዚህ የሠለጠነ ሰው አለመኖሩን ራስህም ታውቃለህና።”

7 ኪራም የሰሎሞን መልእክት በደረሰው ጊዜ እጅግ ደስ ስላለው፣ “ይህን ታላቅ ሕዝብ እንዲመራ ለዳዊት ጥበበኛ ልጅ ሰጥቶታልና ዛሬ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይግባው” አለ።

8 ስለዚህ ኪራም፣ ለሰሎሞን እንዲህ ሲል ላከበት፤“የላክኸው መልእክት ደርሶኛል፤ የዝግባውንና የጥዱን ግንድ በማቅረብ ረገድ የምትፈልገውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ነኝ፤

9 ሰዎቼ ግንዱን ከሊባኖስ እስከ ባሕሩ ድረስ ጐትተው ያወርዳሉ፤ እኔም ግንዱ ሁሉ ታስሮ አንተ እስከ ወሰንኸው ስፍራ በባሕር ተንሳፎ እንዲደርስ አደርጋለሁ፤ እዚያም እኔ እፈታዋለሁ፣ አንተም ትወስደዋለህ፤ አንተም ለቤተ ሰቤ ቀለብ በመስጠት ፍላጎቴን ታሟላለህ።”

10 በዚህ ሁኔታ ኪራም ለሰሎሞን የሚያስፈልገውን የዝግባና የጥድ ግንድ በሙሉ ያቀርብለት ጀመር፤

11 ሰሎሞን ደግሞ ለኪራም ቤተ ሰው ቀለብ እንዲሆን ሃያ ሺህ የቆሮስ መስፈሪያ ስንዴ፣ ሃያ ሺህ ኮር ንጹሕ የወይራ ዘይት ሰጠው፤ ይህን ባለማቋረጥ በያመቱ ለኪራም ይሰጥ ነበር።

12 እግዚአብሔርም በገባለት ተስፋ መሠረት ለሰሎሞን ጥበብን ሰጠው፤ በኪራምና በሰሎሞን መካከልም መልካም ግንኙነት ነበር፤ ሁለቱም ቃል ኪዳን አደረጉ።

13 ንጉሥ ሰሎሞን ከመላው እስራኤል የጒልበት ሠራተኞችን መለመለ፤ ቍጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ነበር።

14 እነዚህንም አንድ ወር በሊባኖስ እንዲሠሩ፣ ሁለት ወር በቤታቸው እንዲያርፉ በማድረግ፣ ዐሥር ዐሥር ሺዉን ወር ተራ አግብቶ ላካቸው። የጒልበት ሠራተኞቹም አለቃ አዶኒራም ነበር።

15 ሰሎሞንም በኰረብታማው አገር ሰባ ሺህ ተሸካሚዎችና ሰማንያ ሺህ ድንጋይ ጠራቢዎች ነበሩት፤

16 እንዲሁም ሥራውን የሚቈጣጠሩ ሦስት ሺህ ሦስት መቶ ኀላፊዎች ነበሩ።

17 እነርሱም በንጉሡ ትእዛዝ ለቤተ መቅደሱ መሠረት የሚሆን ታላላቅና ምርጥ ድንጋይ ፈልፍለው በማውጣት የተጠረበ ድንጋይ አዘጋጁ።

18 የሰሎሞንና የኪራም የእጅ ባለ ሙያዎች እንዲሁም የጌባል ሰዎች ለቤተ መቅደሱ የሚያስፈልገውን ዕንጨትና ድንጋይ ፈልጠው አዘጋጁ።

ምዕራፎች

1 2 3 4 5 6 7 8 9 10 11 12 13 14 15 16 17 18 19 20 21 22