2 ሳሙኤል 20:15-21 NASV

15 ከኢዮአብ ጋር ያለውም ሰራዊት መጥቶ ሳቤዔን በአቤል ቤትመዓካ በኩል ከበበው፤ በስተ ውጭም እስከ ከተማዪቱ ግንብ ጫፍ ድረስ ዙሪያውን የዐፈር ድልድል ሠሩ፤ ግንቡን ለመናድ በኀይል በሚደበድቡበት ጊዜ፣

16 አንዲት ብልኅ ሴት ድምፅዋን ከፍ አድርጋ፣ “ስሙ! ስሙ! ለኢዮአብ የምነግረው ነገር ስላለ ወደዚህ እንዲመጣ ንገሩት” አለቻቸው።

17 ኢዮአብ ወደ እርሷ ሄደ፤ እርሷም፣ “ኢዮአብ አንተ ነህ?’ ስትል ጠየቀችው።እርሱም፣ “አዎን እኔ ነኝ” ብሎ መለሰላት።እርሷም፣ “እንግዲህ አገልጋይህ የምትለውን አድምጥ” አለችው።እርሱም፣ “እሺ፣ አደምጣለሁ” አላት።

18 ከዚያ በመቀጠልም እንዲህ አለች፤ “በቀድሞው ጊዜ ሰዎች፣ ‘ምክርን ከአቤል ጠይቁ’ ይሉ ነበር፤ ታዲያ እንዳሉትም ይፈጸም ነበር፤

19 በእስራኤል ሰላማዊና ታማኝ ከሆኑ ሰዎች መካከል አንዷ እኔ ነኝ፤ አንተ በእስራኤል እናት የሆነችውን ከተማ ለማጥፋት ትሻለህ፤ የእግዚአብሔርን ርስት ለመዋጥ የፈለግኸው ለምንድን ነው?”

20 ኢዮአብም እንዲህ ሲል መለሰ፤ “ይህስ ከእኔ ይራቅ! መዋጡና ማጥፋቱ አሁንም ከእኔ ይራቅ!

21 ነገሩስ እንዲህ አይደለም፤ የኰረብታማው የኤፍሬሙ አገር ሰው፣ የቢክሪ ልጅ ሳቤዔ እጁን በንጉሡ በዳዊት ላይ አንሥቶአል፤ እናንተ ይህን ሰው ብቻ ስጡኝ እንጂ እኔ ከተማዪቱን ትቼ እሄዳለሁ” አላት።ሴቲቱም ኢዮአብን፣ “የሰውየው ራስ ተቈርጦ በግንቡ ላይ ይወረወርልሃል” አለችው።