2 ሳሙኤል

ምዕራፎች 8

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ዳዊት የተቀዳጃቸው ድሎች

1ከዚህ በኋላ ዳዊት ፍልስጥኤማውያንን ድል አደረጋቸው፤ በቍጥጥሩም ሥር አዋላቸው፣ ሜቴግ አማ የተባለችውንም ከተማ ከፍልስጥኤማውያን ቍጥጥር ነጻ አደረጋት። 2እንዲሁም ዳዊት ሞዓባውያንን ድል አደረገ፤ በመሬት ላይ አጋድሞ በገመድ ለካቸው፤ በገመድ ከተለኩትም ሁለት እጅ ሲገድል፣ አንድ እጅ ግን በሕይወት ይተው ነበር። ስለዚህ ሞዓባውያን የዳዊት ተገዦች ሆኑ፤ ገበሩለትም። 3ከዚህም በቀር ዳዊት በኤፍራጥስ ወንዝ አጠገብ ያለውን ግዛት መልሶ ለመያዝ በሄደ ጊዜ፣ የሱባን ንጉሥ የረአብን ልጅ አድርአዛርን ወጋው። 4ዳዊትም አንድ ሺህ ሠረገሎች፣ ሰባት ሺህ ፈረሰኞችና ሃያ ሺህ እግረኞች ማረከበት። ቊጥራቸው መቶ የሆነ የሠረገላ ፈረሶች ብቻ ሲቀሩ ሌሎቹን በሙሉ ቋንጃቸውን ቈረጠ። 5የደማስቆዎቹ ሶርያውያን የሱባን ንጉሥ አድርአዛርን ለመርዳት በመጡ ጊዜ ዳዊት ሃያ ሁለት ሺህ ሰው ገደለባቸው። 6ከዚያም የደማስቆ ክፍል በሆነው የሶርያውያን ግዛት የጦር ሰፈሮችን አቋቋመ። ሶርያውያን ተገዙለት፤ ገበሩለትም። እግዚአብሔርም ዳዊት በሄደበት ሁሉ ድልን ሰጠው። 7ዳዊት የአድርአዛር ሹማምንት ያነገቧቸውን የወርቅ ጋሻዎች ወስዶ ወደ ኢየሩሳሌም አመጣቸው። 8ንጉሡ ዳዊት ቤጣህና ቤሮታይ ከተባሉ ከአድርአዛር ከተሞችም እጅግ ብዙ ናስ አጋዘ። 9የሐማት ንጉሥ ቶዑ ዳዊት መላውን የአድርአዛርን ሰራዊት ማሸነፉን በሰማ ጊዜ፣ 10ቶዑ ከአድርአዛር ጋር ሁል ጊዜ ይዋጋ ስለ ነበር፣ ሰላምታና በአድርአዛር ላይ ሰለተቀዳጀውም ድል የደስታ መግለጫ እንዲያቀርብለት፣ ልጁን ዮራምን ወደ ንጉሥ ዳዊት ላከው፤ እርሱም የብር፣ የወርቅና የናስ ዕቃ ይዞ መጣ። 11ንጉሥ ዳዊትም፣ ቀድሞ ካስገበራቸው መንግሥታት ሁሉ በገባለት ብርና ወርቅ እንዳደረገው እነዚህንም ዕቃዎች ለእግዚአብሔር ቀደሳቸው። 12የገበሩትም መንግሥታት ኤዶምና ሞዓብ፣ አሞናውያን፣ ፍልስጥኤማውያንና አማሌቃውያን ነበሩ። እንዲሁም ከሱባ ንጉሥ ከረአብ ልጅ ከአድርአዛር የወሰደውን ምርኮ ለእግዚአብሔር ቀደሰ። 13ዳዊት የጨው ሸለቆ በተባለው ስፍራ ዐሥራ ስምንት ሺህ ኤዶማውያንን ገድሎ ከተመለሰ በኋላ ስሙ ገነነ። 14በመላው ኤዶም የጦር ሰፈሮችን አቋቋመ፤ ኤዶማውያን ሁሉ ለዳዊት ተገዙ፤ እግዚአብሔርም ዳዊት በሄደበት ስፍራ ሁሉ ድልን ሰጠው።

የዳዊት ሹማምት

15ዳዊት በመላው እስራኤል ላይ ነገሠ፤ ለሕዝቡም ሁሉ ፍትሕና ርትዕ አሰፈነላቸው። 16የጽሩያ ልጅ ኢዮአብ የሰራዊቱ አለቃ ሲሆን፣ የአሒሉድ ልጅ ኢዮሣፍጥም ታሪክ ጸሓፊ ነበረ። 17እንዲሁም የአኪጦብ ልጅ ሳዶቅና የአብያታር ልጅ አቢሜሌክ ካህናት ሲሆኑ፣ ሠራያ ጸሓፊ ነበረ፤ 18የዮዳሔ ልጅ በናያስ የከሪታውያንና የፈሊታውያን አለቃ ሲሆን፣ የዳዊት ወንዶች ልጆች ደግሞ የቤተ መንግሥት አማካሪዎች ነበሩ።