ዘፀአት 14:23-29 NASV

23 ግብፃውያንም አሳደዷቸው፤ የፈርዖን ፈረሶች፣ ሰረገሎችና ፈረሰኞች በሙሉ ተከትለዋቸው ወደ ባሕሩ ገቡ።

24 ሲነጋጋም እግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳትና በደመና ዓምድ ሆኖ የግብፃውያንን ሰራዊት ቍልቍል ተመለከተ፤ በግብፃውያን ሰራዊት ላይም ሽብር ላከባቸው።

25 መንዳት እንዳይችሉም የሠረገላዎቹን መሽከርከሪያዎች አቈላለፈባቸው ግብፃውያኑም፣ “ከእስራኤላውያን እንሽሽ! እግዚአብሔር (ያህዌ) ግብፅን እየተዋጋላቸው ነው” አሉ።

26 ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን፣ “ውሃው ግብፃውያንን ሠረገሎቻቸውንና ፈረሰኞቻቸውን ተመልሶ እንዲሸፍናቸው እጅህን በባሕሩ ላይ ዘርጋ” አለው።

27 ሙሴም እጁን በባሕሩ ላይ ዘረጋ፤ ንጋት ላይም ባሕሩ ወደ ቀድሞ ቦታው ተመለሰ። ግብፃውያን ከውሃው ሸሹ፤ እግዚአብሔርም (ያህዌ) ግብፃውያንን በባሕሩ ውስጥ ጣላቸው።

28 ውሃውም ተመልሶ እስራኤላውያንን ተከትለው ወደ ባሕሩ የገቡትን ሠረገሎች፣ ፈረሰኞች፣ መላውን የግብፅ ሰራዊት ሁሉ ሸፈነ። አንድም እንኳ አልተረፈም።

29 እስራኤላውያን ግን ውሃው ግራና ቀኝ እንደ ግድግዳ ሆኖ፣ በደረቅ ምድር ባሕሩን ተሻገሩ።