20 “ ‘ለእኔ የወለድሻቸውን ወንዶችና ሴቶች ልጆችሽን እንዲበሏቸው ለምስሎቹ ሠዋሽላቸው፤ አመንዝራነትሽ አንሶ ነውን?
21 ልጆቼን ዐርደሽ ለጣዖት መሥዋዕት አድርገሽ አቀረብሻቸው።
22 በእነዚህ አስጸያፊ ተግባሮችሽና አመንዝራነትሽ ሁሉ፣ ከእናትሽ ማሕፀን እንደ ወጣሽ ዕርቃንሽን ሆነሽ በደምሽ ውስጥ ስትንፈራገጪ የነበርሽበት የሕፃንነትሽ ወራት ትዝም አላለሽ!።
23 “ ‘ወዮ! ወዮልሽ! ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ከሌላው ክፋትሽ ሁሉ በተጨማሪ፣
24 ለራስሽ ጒብታን አበጀሽ፤ በየአደባባዩም የማምለኪያ ኰረብታ ሠራሽ።
25 በየመንገዱ መጠምዘዣ ላይም የመስገጃ ኰረብታ አበጀሽ፤ ገላሽን ለዐላፊ አግዳሚው በማቅረብና አመንዝራነትሽን በማበራከት ውበትሽንም አረከስሽ።
26 ዘማውያን ከሆኑ ግብፃውያን ጎረቤቶችሽ ጋር አመነዘርሽ፤ ገደብ በሌለው የዝሙት ተግባርሽም ለቍጣ አነሣሣሽኝ።