ሕዝቅኤል

ምዕራፎች 19

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ስለ እስራኤል መሳፍንት የወጣ ሙሾ

1“ስለ እስራኤል መሳፍንት ሙሾ አውጣ፤ 2እንዲህም በል፤“ ‘እናትህ በአንበሶች መካከል እንዴትያለች አንበሳ ነበረች!በደቦል አንበሶች መካከል ተጋደመች፤ግልገሎቿንም በዚያ አሳደገች። 3ከግልገሎቿ መካከል አንዱን አሳደገችው፤እርሱም ብርቱ አንበሳ ሆነ።ግዳይ መንጠቅን ተማረ፤ሰዎችንም በላ። 4አሕዛብም ስለ እርሱ ሰሙ፤በጒድጓዳቸውም ገብቶ ተያዘ፤እነርሱም በስናግ ጐትተው፣ወደ ግብፅ ምድር ወሰዱት። 5“ ‘ተስፋዋ መጨናገፉን፣የጠበቀችውም አለመሳካቱን ባየች ጊዜ፣ከግልገሎቿ ሌላውን ወስዳ፣ብርቱ አንበሳ አድርጋ አሳደገችው። 6እርሱም በአንበሶች መካከል ተጐማለለ፤እየበረታም ሄደ፤ግዳይ መንጠቅን ተማረሰዎችንም በላ። 7ምሽጎቻቸውን አወደመ፤ከተሞቻቸውንም ባድማ አደረገ፤ምድሪቷና በውስጧ ያሉት ሁሉ፣ከግሣቱ የተነሣ ተንቀጠቀጡ። 8በዙሪያው ያሉ አሕዛብ ተነሡበት፤ከየአገሩም ሁሉ ተሰበሰቡበት፤መረባቸውን ዘረጉበት፤በጒድጓዳቸውም ገብቶ ተያዘ። 9በስናግም በመጐተት ቀፎ ውስጥ ከተው፣ወደ ባቢሎን ንጉሥ አመጡት፤ድምፁ በእስራኤል ተራሮች ላይ፣ዳግመኛ እንዳይሰማ፣በእስር ቤት አኖሩት። 10“ ‘እናትህ በውሃ አጠገብ የተተከለ፣በዕርሻ ውስጥ ያለ፣ከውሃም ብዛት የተነሣ፣ያፈራና የተንሰራፋ የወይን ተክልመሰለች። 11ቅርንጫፎቿ ለበትረ መንግሥትየሚሆኑ፣ ጠንካሮች ነበሩ፤ጥቅጥቅ ባሉ ቅጠሎች መካከል፣በቁመቷና በብዙ ቅርንጫፎቿ፣ዘለግ ብላ፣ ጐልታ ትታይ ነበር። 12ነገር ግን በቍጣ ተነቀለች፤ወደ ምድርም ተጣለች።የምሥራቅ ነፋስ አደረቃት፤ፍሬዎቿንም አረገፈባት።ብርቱዎቹ ቅርንጫፎቿ ክው አሉ፤እሳትም በላቸው። 13አሁን ውሃ በተጠማ ደረቅ ምድር፣በበረሓ ውስጥ ተተከለች። 14ከዋና ቅርንጫፎቿ ከአንዱ እሳት ወጣ፤ፍሬዋንም በላ።በትረ መንግሥት የሚሆን፣አንድም ጠንካራ ቅርንጫፍ አልተረፈም።’ይህ ሙሾ ነው፤ ለሐዘን እንጒርጒሮም ይሆናል።’