ኢሳይያስ 49:21-26 NASV

21 በልብሽም እንዲህ ትያለሽ፣‘እነዚህን የወለደልኝ ማን ነው?እኔ ሐዘንተኛና መካን፣የተሰደድሁና የተጠላሁ ነበርሁ፤እነዚህን ማን አሳደጋቸው?ብቻዬን ቀርቼ ነበር፤ታዲያ፣ እነዚህ ከየት መጡ?’

22 ልዑል እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እነሆ፤ አሕዛብን በጥቅሻ እጣራለሁ፤ዐርማዬንም ለሕዝቦች ከፍ አደርጋለሁ፤ወንዶች ልጆችሽን በዕቅፋቸው ያመጡልሻል፤ሴቶች ልጆችሽንም በትከሻቸው ይሸከሙልሻል።

23 ነገሥታት አሳዳጊ አባቶችሽ፣እቴጌዎቻቸው ሞግዚቶችሽ ይሆናሉ፤በግንባራቸው ተደፍተው ይሰግዱልሻል፤የእግርሽን ትቢያ ይልሳሉ፤አንቺም እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቂያለሽ፤እኔን ተስፋ የሚያደርጉም አያፍሩም።”

24 ከተዋጊ ብዝበዛ ማስጣል፣ከጨካኝስ ምርኮኞችን ማዳን ይቻላልን?

25 እግዚአብሔር ግን እንዲህ ይላል፤“ከተዋጊዎች ላይ ምርኮኞች በርግጥ ይወሰዳሉ፤ከጨካኞችም ላይ ምርኮ ይበዘበዛል፤ከአንቺ ጋር የሚጣሉትን እጣላቸዋለሁ፤ልጆችሽንም እታደጋለሁ።

26 አስጨናቂዎችሽ የራሳቸውን ሥጋ እንዲበሉ አደርጋቸዋለሁ፤በወይን ጠጅ እንደሚሰከር ሁሉ፣ በገዛ ደማቸው ይሰክራሉ።ከዚያም የሰው ዘር ሁሉ፣እኔ እግዚአብሔር አዳኝሽ፣ታዳጊሽም የያዕቆብ ኀያል እንደሆንሁ ያውቃል።”