ሉቃስ

ምዕራፎች 4

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

የኢየሱስ መፈተን

1ኢየሱስ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ ከዮርዳኖስ እንደ ተመለሰ መንፈስ ወደ በረሓ ወሰደው፤ 2በዚያም አርባ ቀን በዲያብሎስ ተፈተነ፤ በእነዚያም ቀናት ምንም ሳይበላ ቈይቶ በመጨረሻ ተራበ። 3ዲያብሎስም፣ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፣ እስቲ ይህ ድንጋይ እንጀራ እንዲሆን እዘዘው” አለው። 4ኢየሱስም፣ “ ‘ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም’ ተብሎ ተጽፎአል” ብሎ መለሰለት። 5ከዚያም ዲያብሎስ ወደ አንድ ከፍታ ቦታ አውጥቶት የዓለምን መንግሥታት ሁሉ በቅጽበት አሳየው፤ 6እንዲህም አለው፤ “የእነዚህ መንግሥታት ሥልጣንና ክብር ሁሉ ለእኔ ተሰጥቶአል፤ እኔም ለምወደው ስለምሰጥ፣ ለአንተ እሰጥሃለሁ፤ 7ስለዚህ ብትሰግድልኝ ይህ ሁሉ የአንተ ይሆናል።” 8ኢየሱስም መልሶ፣ “ ‘ለጌታ ለአምላክህ ስገድ፤ እርሱንም ብቻ አምልክ’ ተብሎ ተጽፎአል” አለው። 9ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም ወስዶ በቤተ መቅደስ ጒልላት ላይ አቆመውና እንዲህ አለው፤ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፣ እስቲ ራስህን ከዚህ ወደ ታች ወርውር፤ 10ምክንያቱም እንዲህ ተብሎ ተጽፎአል፤“ ‘ይጠብቁህ ዘንድ፣መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋል፤ 11እግርህም ከድንጋይ ጋር እንዳይጋጭ፣በእጆቻቸው ወደ ላይ አንሥተው ይይዙሃል።’ ” 12ኢየሱስም፣ “ ‘ጌታ አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎአል” ብሎ መለሰለት። 13ዲያብሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ ሌላ አመቺ ጊዜ እስኪያገኝ ድረስ ከእርሱ ተለየ።

ኢየሱስ በናዝሬት ተቀባይነት ማጣቱ

14ኢየሱስም በመንፈስ ኀይል ወደ ገሊላ ተመለሰ፤ ዝናውም በአካባቢው ባለው አገር ሁሉ ወጣ። 15እርሱም በምኵራባቸው ያስተምር ነበር፤ ሰውም ሁሉ ያመሰግነው ነበር። 16ከዚያም ወዳደገበት ከተማ ወደ ናዝሬት መጣ፤ እንደ ልማዱም በሰንበት ወደ ምኵራብ ገባ፤ ሊያነብም ተነሥቶ ቆመ። 17የነቢዩ ኢሳይያስ ጥቅልል መጽሐፍም ተሰጠው፤ ጥቅልሉንም መጽሐፍ በተረተረው ጊዜ እንዲህ ተብሎ የተጻፈበትን ክፍል አገኘ፤ 18 “የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፤ ለድኾች ወንጌልን እንድሰብክ፣ እርሱ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩት መፈታትን፣ ለታወሩትም ማየትን እንዳውጅ፣ የተጨቈኑትን ነጻ እንዳወጣ፣ 19 የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እንዳውጅ ልኮኛል።” 20ከዚያም መጽሐፉን ጠቅልሎ ለአገልጋዩ መልሶ ሰጠውና ተቀመጠ፤ በምኵራብ የነበሩትም ሁሉ ትኵር ብለው ይመለከቱት ነበር። 21እርሱም፣ “ይህ በጆሮአችሁ የሰማችሁት የመጽሐፍ ቃል ዛሬ ተፈጸመ” ይላቸው ጀመር። 22ሁሉም ስለ እርሱ በበጎ ይናገሩ ነበር፤ ደግሞም ከአንደበቱ በሚወጣ የጸጋ ቃል እየተገረሙ፣ “ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?” ይሉ ነበር። 23እርሱም፣ “ ‘ባለ መድኀኒት ሆይ፤ ራስህን ፈውስ፤ በቅፍርናሆም ስታደርግ የሰማነውን ነገር እዚህ በራስህ ከተማ ደግሞ አድርግ’ የሚለውን ምሳሌ እንደምትጠቅሱብኝ ጥርጥር የለውም” አላቸው። 24ደግሞም እንዲህ አላቸው፤ “እውነት እላችኋለሁ፤ ነቢይ በገዛ አገሩ አይከበርም። 25ነገር ግን እውነት እላችኋለሁ፤ ሰማይ ሦስት ዓመት ከመንፈቅ ተዘግቶ ጽኑ ራብ በምድሪቱ ሁሉ ላይ በነበረበት በኤልያስ ዘመን፣ ብዙ መበለቶች በእስራኤል ነበሩ፤ 26ኤልያስ ከእነዚህ መካከል ወደ አንዷም አልተላከም፤ ነገር ግን በሲዶና አገር በሰራፕታ ወደ ነበረችው መበለት ተላከ። 27በነቢዩ በኤልሳዕ ዘመንም በእስራኤል ብዙ ለምጻሞች ነበሩ፤ ነገር ግን ከሶርያዊው ከንዕማን በቀር ከእነዚያ መካካል ማንም አልነጻም።” 28በምኵራብ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ይህን በሰሙ ጊዜ በቍጣ ገነፈሉ፤ 29ከተቀመጡበትም ተነሥተው ከከተማው አስወጡት፤ ቊልቊል ሊጥሉትም ከተማቸው ወደ ተሠራች በት ኰረብታ አፋፍ ወሰዱት፤ 30እርሱ ግን በመካከላቸው ሰንጥቆ ሄደ።

ኢየሱስ ርኩስ መንፈስ አስወጣ

31ከዚያም በገሊላ አውራጃ ወደምትገኘው ከተማ ወደ ቅፍርናሆም ወረደ፤ በዚያም በሰንበት ዕለት ሕዝቡን ያስተምር ጀመር፤ 32የሚናገረው በሥልጣን ስለ ነበር በትምህርቱ ተደነቁ። 33በምኵራብም የርኩስ ጋኔን መንፈስ ያደረበት ሰው ነበረ፤ እርሱም ከፍ ባለ ድምፅ ጮኾ፣ 34“ወዮ! የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይ፤ ምን የሚያገናኘን ጉዳይ አለ? የመጣኸው ልታጠፋን ነውን? አንተ ማን እንደሆንህ ዐውቃለሁ፤ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱስ ነህ!” አለው። 35ኢየሱስም፣ “ጸጥ ብለህ ከዚህ ሰው ውጣ!” ብሎ ገሠጸው። ጋኔኑም ሰውየውን በሕዝቡ ሁሉ ፊት ጣለውና ምንም ጒዳት ሳያደርስበት ለቆት ወጣ። 36ሰዎቹም ሁሉ ተገረሙ፤ እርስ በእርሳቸውም፣ “ለመሆኑ ይህ ትምህርት ምንድን ነው? በሥልጣንና በኀይል ርኩሳን መናፍስትን ያዛል፤ እነርሱምኮ ይወጣሉ” ተባባሉ። 37የእርሱም ዝና በአካባቢው ወዳለው ስፍራ ሁሉ ወጣ።

ኢየሱስ ብዙ በሽተኞችን ፈወሰ

38ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ከምኵራብ ወጥቶ ወደ ስምዖን ቤት ገባ። የስምዖንም አማት ኀይለኛ ትኵሳት ይዞአት ታማ ነበር፤ እንዲፈውሳትም ስለ እርሷ ለመኑት። 39እርሱም ወደ ተኛችበት ጠጋ ብሎ በማጐንበስ ትኵሳቱን ገሠጸው፤ ትኵሳቱም ለቀቃትና ወዲያው ተነሥታ አስተናገደቻቸው። 40ፀሓይ መጥለቂያ ላይም፣ የተለያየ ሕመም ያደረባቸውን ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ አመጡ፤ እርሱም በእያንዳንዳቸው ላይ እጁን ጭኖ ፈወሳቸው። 41አጋንንትም ደግሞ፣ “አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ!” እያሉና እየጮኹ ከብዙ ሰዎች ወጡ። እርሱ ግን ገሠጻቸው፤ ክርስቶስ መሆኑንም ያውቁ ስለ ነበር፣ አንዳች እንዲናገሩ አልፈቀደላቸውም። 42ሲነጋም ኢየሱስ ወደ አንድ ገለልተኛ ስፍራ ሄደ፤ ሕዝቡም ይፈልጉት ነበር፤ እርሱ ወዳለበትም ቦታ መጡ፤ ከእነርሱ ተለይቶ እንዳይሄድ ሊከለክሉት ሞከሩ። 43እርሱ ግን፣ “ወደ ሌሎቹም ከተሞች ሄጄ የእግዚአብሔርን መንግሥት ወንጌል መስበክ ይገባኛል፤ የተላክሁት ለዚሁ ዐላማ ነውና” አላቸው። 44በይሁዳ ምኵራቦችም መስበኩን ቀጠለ።