ኤርምያስ 2:1-7 NASV

1 የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

2 “ሂድና ጮኸህ ይህን ለኢየሩሳሌም ጆሮ አሰማ፤“እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤‘በወጣትነትሽ ጊዜ የነበረሽን ታማኝነት፣በሙሽርነትሽም ወራት እንዴት እንደ ወደድሽኝ፣በምድረ በዳ ዘር በማይዘራበት ምድር፣እንዴት እንደተከተልሽኝ አስታውሳለሁ።

3 እስራኤል ለእግዚአብሔር ቅዱስ ነበረች፤የመከሩም በኵር ነበረች፤የዋጧት ሁሉ በደለኞች ሆኑ፤መዓትም ደረሰባቸው’ ”ይላል እግዚአብሔር።

4 የያዕቆብ ቤት ሆይ፤ የእስራኤል ቤት ወገን ሁላችሁ፣ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ።

5 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“አባቶቻችሁ ከእኔ የራቁት፣ከንቱ ነገርን የተከተሉት፣ራሳቸውም ከንቱ የሆኑት፣ምን ጥፋት አግኝተውብኝ ነው?

6 እነርሱም፣ ‘ከግብፅ ምድር ያወጣን፣በወና ምድረ በዳ፣በጐድጓዳና በበረሓ መሬት፣በደረቅና በጨለማ ቦታ፣ሰው በማያልፍበትና በማይኖርበት ስፍራ፣የመራን እግዚአብሔር ወዴት ነው?’ ብለው አልጠየቁም።

7 እኔ፣ ፍሬዋንና በረከቷን እንድትበሉ፣ለም ወደ ሆነ መሬት አመጣኋችሁ፤እናንተ ግን መጥታችሁ ምድሬን አረከሳችሁ፤ርስቴንም ጸያፍ አደረጋችሁ።