ኤርምያስ 23:2-8 NASV

2 ስለዚህ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሕዝቤን ስለሚጠብቁ እረኞች እንዲህ ይላል፤ “መንጋዬን ስለ በተናችሁ፣ ስላባረራችሁና ተገቢውን ጥንቃቄ ስላላደረጋችሁላቸው፣ ለክፋታችሁ ተገቢውን ቅጣት አመጣባችኋለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤

3 “የመንጋዬንም ቅሬታ ካባረርሁባቸው አገሮች ሁሉ እኔ ራሴ ሰብስቤ፣ ወደ መሰማሪያቸው እመልሳቸዋለሁ፤ በዚያም ፍሬያማ ይሆናሉ፤ ይበዛሉም።

4 የሚጠብቋቸውን እረኞች አስነሣላቸዋለሁ፤ ከእንግዲህም አይፈሩም፤ አይደነግጡም ከእነርሱም አንድ እንኳ አይጐድልም” ይላል እግዚአብሔር።

5 “እነሆ፤ ለዳዊት፣ጻድቅ ቅርንጫፍ የማስነሣበት ጊዜ ይመጣል፤እርሱም ፍትሕንና ጽድቅን የሚያደርግ፣በጥበብ የሚገዛ ንጉሥ ይሆናል” ይላል እግዚአብሔር።

6 በእርሱም ዘመን ይሁዳ ይድናል፤እስራኤልም በሰላም ይኖራል፤የሚጠራበትም ስም፣‘እግዚአብሔር ጽድቃችን’ የሚል ነው።

7 “ስለዚህ ሰዎች፣ ‘እስራኤላውያንን ከግብፅ ምድር ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን!’ ብለው ከእንግዲህ የማይምሉበት ዘመን ይመጣል” ይላል እግዚአብሔር፤

8 ነገር ግን፣ ‘እስራኤልን ከሰሜን ምድርና እነርሱን ከበተነባቸው ከሌሎች አገሮች ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን’ ይላሉ፤ ከዚያ በኋላ በገዛ ምድራቸው ይኖራሉ።