ኤርምያስ 34:12-18 NASV

12 ስለዚህ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤርምያስ እንዲህ ሲል መጣ፤

13 “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ በባርነት ከተገዙበት ከግብፅ ምድር ባወጣኋቸው ጊዜ፣ ከአባቶቻችሁ ጋር እንዲህ ብዬ ቃል ኪዳን አደረግሁ፤

14 ‘ራሱን በባርነት ለእናንተ የሸጠውን ዕብራዊ ወንድማችሁን እያንዳንዳችሁ በየሰባት ዓመቱ ነጻ ትለቃላችሁ፤ ስድስት ዓመት ከተገዛላችሁ በኋላ ነጻ ታወጡታላችሁ።’ አባቶቻችሁ ግን አልሰሙኝም ጆሮአቸውንም ወደ እኔ አላዘነበሉም።

15 እናንተም አሁን ንስሓ በመግባት በፊቴ ትክክለኛ ነገር አደረጋችሁ፤ እያንዳንዳችሁም ለወገኖቻችሁ ነጻነት ዐወጃችሁ፤ ስሜ በሚጠራበት ቤትም በፊቴ ቃል ኪዳን ገባችሁ።

16 ነገር ግን ተመልሳችሁ ስሜን አረከሳችሁ፤ ወደ ፈለጉበት እንዲሄዱ ነጻ የለቀቃችኋቸውንም ወንዶችና ሴቶች ባሪያዎቻችሁን መለሳችሁ፤ እንደ ገናም ባሪያዎቻችሁ አደረጋችኋቸው።

17 “ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ለወንድሞቻችሁና ለወገኖቻችሁ ነጻነት አላወጃችሁምና አልታዘዛችሁኝም። እንግዲህ እኔ ‘ነጻነት’ ዐውጅላችኋለሁ፤ ይላል እግዚአብሔር። ይኸውም በሰይፍ፣ በቸነፈርና በራብ የምትወድቁበት ‘ነጻነት’ ነው። ለምድር መንግሥታት ሁሉ መሠቀቂያ አደርጋችኋለሁ።

18 ኪዳኔን ያፈረሱትንና በፊቴ የገቡትን የኪዳኑን ቃል ያልፈጸሙትን ሰዎች ሥጋውን ሁለት ቦታ ከፍለው በመካከሉ እንዳለፉት፣ እንደ እንቦሳው አደርጋቸዋለሁ።