ኤርምያስ 34:9-15 NASV

9 እያንዳንዱ ሰው፣ ዕብራዊ የሆነውን ወንድ ባሪያውንና ዕብራዊት የሆነችውን ሴት ባሪያውን ነጻ ማውጣት ነበረበት፤ ማንም ሰው አይሁዳዊ ወንድሙን በባርነት መግዛት አልነበረበትም።

10 በዚህ ቃል ኪዳን የተስማሙት ባለሥልጣኖችና ሕዝቡ ሁሉ ወንድ ወይም ሴት ባሪያዎቻቸውን ነጻ ለመልቀቅና ከእንግዲህ ባሪያ አድርገው ላይገዟቸው ተስማሙ።

11 በኋላ ግን ሐሳባቸውን ቀይረው ነጻ የለቀቋቸው ባሪያዎቻቸውን እንዲመለሱ አደረጓቸው፤ እንደ ገናም ባሪያ አድርገው ገዟቸው።

12 ስለዚህ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤርምያስ እንዲህ ሲል መጣ፤

13 “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ በባርነት ከተገዙበት ከግብፅ ምድር ባወጣኋቸው ጊዜ፣ ከአባቶቻችሁ ጋር እንዲህ ብዬ ቃል ኪዳን አደረግሁ፤

14 ‘ራሱን በባርነት ለእናንተ የሸጠውን ዕብራዊ ወንድማችሁን እያንዳንዳችሁ በየሰባት ዓመቱ ነጻ ትለቃላችሁ፤ ስድስት ዓመት ከተገዛላችሁ በኋላ ነጻ ታወጡታላችሁ።’ አባቶቻችሁ ግን አልሰሙኝም ጆሮአቸውንም ወደ እኔ አላዘነበሉም።

15 እናንተም አሁን ንስሓ በመግባት በፊቴ ትክክለኛ ነገር አደረጋችሁ፤ እያንዳንዳችሁም ለወገኖቻችሁ ነጻነት ዐወጃችሁ፤ ስሜ በሚጠራበት ቤትም በፊቴ ቃል ኪዳን ገባችሁ።