ኤርምያስ 43:1-7 NASV

1 ኤርምያስ፣ እግዚአብሔር ለእነርሱ እንዲነግራቸው የላከውን የአምላካቸውን የእግዚአብሔርን ቃል ሁሉ ለሕዝቡ ተናግሮ በጨረሰ ጊዜ፣

2 የሆሽያ ልጅ ዓዛርያስ፣ የቃሬያ ልጅ ዮሐናንና ትዕቢተኞች የሆኑ ሰዎች ሁሉ ኤርምያስን እንዲህ አሉት፤ “ትዋሻለህ! አምላካችን እግዚአብሔር፣ ‘እዚያ ለመኖር ወደ ግብፅ አትሂዱ ብለህ ንገራቸው’ ብሎ አልላከህም፤

3 ነገር ግን ባቢሎናውያን እንዲገድሉን ወይም ማርከው ወደ ባቢሎን እንዲወስዱን ለእነርሱ አሳልፈህ ትሰጠን ዘንድ የኔርያ ልጅ ባሮክ በእኛ ላይ አነሣሥቶሃል።”

4 ስለዚህ የቃሬያ ልጅ ዮሐናንና፣ የጦር መኰንኖቹ ሁሉ እንዲሁም ሕዝቡ በሙሉ እግዚአብሔር በይሁዳ ምድር እንዲቀመጡ ያዘዛቸውን ቃል አልሰሙም።

5 ነገር ግን፣ የቃሪያ ልጅ ዮሐናንና የጦር መኮንኖቹ ሁሉ፣ በይሁዳ ምድር ለመቀመጥ ከተበተኑበት ከአሕዛብ ሁሉ መካከል የተመለሱትን የይሁዳን ቅሬታዎች ሁሉ ይዘው ሄዱ፤

6 በተጨማሪም ወንዶችን፣ ሴቶችንና ሕፃናትን እንዲሁም የክብር ዘበኞች አዛዥ ናቡዘረዳን በአኪቃም ልጅ በጎዶልያስ እጅ የተዋቸውን የንጉሡን ሴቶች ልጆች፣ ነቢዩ ኤርምያስንና የኔርያን ልጅ ባሮክን ወሰዷቸው፤

7 የእግዚአብሔርንም ቃል ባለመታዘዝ ወደ ግብፅ ገቡ፤ ዘልቀውም እስከ ጣፍናስ ድረስ ሄዱ።