ዘሌዋውያን

ምዕራፎች 27

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ስለ ስጦታ የወጣ ሕግ

1 እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤ 2“ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ተናገር፤ ‘ማንኛውም ሰው ተመጣጣኙን ዋጋ በመክፈል ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰውን ለመስጠት የተለየ ስእለት ቢሳል፣ 3ዕድሜው ከሃያ እስከ ሥልሳ ዓመት ለሆነ ወንድ፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መሠረት፣ ግምቱ አምሳ ጥሬ ሰቅል ብር ይሁን። 4ለሴት ከሆነ ግምቱ ሠላሳ ሰቅል ይሁን። 5ዕድሜው ከአምስት እስከ ሃያ ዓመት ለሆነ ሰው፣ ወንድ ከሆነ ግምቱ ሃያ ሰቅል፣ ሴት ከሆነች ግምቷ ዐሥር ሰቅል ይሁን። 6ዕድሜው ከአንድ ወር እስከ አምስት ዓመት ለሆነ ሰው፣ ወንድ ከሆነ ግምቱ አምስት ሰቅል ጥሬ ብር፣ ለሴት ከሆነ ሦስት ሰቅል ጥሬ ብር ይሁን። 7ሥልሳ ዓመት ወይም ከዚያ በላይ ለሆነ ሰው፣ ወንድ ከሆነ ግምቱ ዐሥራ አምስት ሰቅል፣ ሴት ከሆነች ዐሥር ሰቅል ይሁን። 8ስእለት የተሳለው ድኻ ከሆነና ግምቱን መክፈል ካልቻለ ግን፣ ለስጦታ ያሰበውን ሰው ወደ ካህኑ ያምጣ፤ ካህኑም የተሳለው ሰው ባለው ዐቅም መሠረት መክፈል የሚገባውን ይተምንለታል። 9“ ‘ሰውየው የተሳለው ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መሥዋዕት ሆኖ መቅረብ የሚችል እንስሳ ከሆነ፣ እንዲህ ያለው ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተሰጠ እንስሳ የተቀደሰ ይሆናል። 10ሰውየው መልካም የሆነውን እንስሳ መልካም ባልሆነው፣ መልካም ያልሆነውንም መልካም በሆነው አይለውጥ ወይም አይተካ፤ አንዱን እንስሳ በሌላው ከተካም ሁለቱ የተቀደሱ ይሆናሉ። 11እንስሳው በሥርዐቱ መሠረት የረከሰ፣ ለእግዚአብሔርም (ያህዌ) መሥዋዕት ሆኖ መቅረብ የማይገባው ከሆነ፣ ሰውየው እንስሳውን ወደ ካህኑ ያቅርብ፤ 12መልካም ቢሆን ወይም ባይሆን፣ ካህኑ ዋጋውን ይወስን፤ የካህኑም ውሳኔ የጸና ይሆናል። 13ባለቤቱ እንስሳውን መዋጀት ከፈለገ ግን፣ በተተመነው ዋጋ ላይ አንድ አምስተኛ መጨመር አለበት። 14“ ‘አንድ ሰው ቤቱን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ይሆን ዘንድ ቢቀድስ፣ መልካም ቢሆን ወይም ባይሆን ካህኑ ዋጋውን ይተምን፤ ካህኑም የተመነው ዋጋ የጸና ይሆናል። 15ቤቱን የቀደሰው ሰው መልሶ ሊዋጀው ከፈለገ ግን፣ የዋጋውን አንድ አምስተኛ በዋጋው ላይ መጨመር አለበት፤ ቤቱም ዳግመኛ የራሱ ይሆናል። 16“ ‘አንድ ሰው ከወረሰው ርስት ላይ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የዕርሻ መሬት ቢቀድስ፣ ዋጋው የሚተመነው ለመሬቱ በሚያስፈልገው ዘር መጠን ይሆናል፤ ይኸውም ለአንድ ሆሜር መስፈሪያ የገብስ ዘር አምሳ ሰቅል ጥሬ ብር ነው። 17ሰውየው ዕርሻውን የቀደሰው በኢዮቤልዩ ዓመት ከሆነ፣ የተወሰነው ዋጋ አይለወጥም። 18ዕርሻውን የሚቀድሰው ከኢዮቤልዩ በኋላ ከሆነ ግን፣ ካህኑ ዋጋውን የሚተምነው እስከሚመጣው የኢዮቤልዩ ዓመት ድረስ ባሉት ዓመታት ቍጥር ልክ ነው፤ የተተመነውም ዋጋ ይቀነሳል። 19ዕርሻውን የቀደሰው ሰው መልሶ መዋጀት ከፈለገ፣ በዋጋው ላይ አንድ አምስተኛ መጨመር አለበት፤ ከዚያ በኋላ ዕርሻው እንደ ገና የራሱ ይሆናል። 20ዕርሻውን ባይዋጅ ወይም ለሌላ ሰው አሳልፎ ቢሸጥ፣ ከዚያ በኋላ ሊዋጀው አይችልም። 21እርሻው በኢዮቤልዩ በሚለቀ ቅበት ጊዜ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) እንደተሰጠ ዕርሻ ተቈጥሮ ቅዱስና የካህናቱ ንብረት ይሆናል። 22“ ‘አንድ ሰው የወረሰው ርስት ያልሆነውን፣ በገንዘቡ የገዛውን የዕርሻ መሬት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ቢቀድስ፣ 23ካህኑ የእርሻውን መሬት ዋጋ እስከ ኢዮቤልዩ ዓመት ድረስ ባለው ጊዜ መጠን ይተምናል፤ ሰውየው የተተመነውን ዋጋ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተቀደሰ አድርጎ በዚያኑ ዕለት ይክፈል። 24በኢዮቤልዩ ዓመትም የዕርሻው መሬት የቀድሞው ባለ ርስት ለነበረው፣ ለሸጠውም ሰው ይመለሳል። 25እያንዳንዱ ዋጋ የሚተመነው በቤተ መቅደሱ ሰቅል ልክ ሆኖ አንዱ ሰቅል ሃያ ጌራ ነው። 26“ ‘የእንስሳት በኵር ቀድሞውኑ የእግዚአብሔር (ያህዌ) ስለ ሆነ፣ ማንም ሰው የእንስሳትን በኵር ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መቀደስ አይችልም፤ በሬም ሆነ በግ የእግዚአብሔር (ያህዌ) ነውና። 27እንስሳው ርኩስ ከሆነ ግን፣ ባለቤቱ በተተመነው ዋጋ ላይ አንድ አምስተኛ ጨምሮ ሊዋጀው ይችላል፤ የማይዋጀው ከሆነ ግን በተተመነው ዋጋ ይሸጥ። 28“ ‘ነገር ግን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ተለይቶ የተሰጠ ማንኛውም ነገር፦ ሰውም ሆነ እንስሳ ወይም በውርስ የተገኘ መሬት አይሸጥም፤ አይዋጅምም። ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተሰጠ ማንኛውም ነገር እጅግ የተቀደሰ ነውና። 29“ ‘እንዲጠፋ የተወሰነ ማንኛውም ሰው አይዋጅም፤ መገደል አለበት። 30“ ‘ከዕርሻ ምርትም ሆነ ከዛፍ ፍሬ፣ ማንኛውም ከምድሪቱ የሚገኝ ዐሥራት የእግዚአብሔር (ያህዌ) ነው፤ ለእግዚአብሔርም (ያህዌ) የተቀደሰ ነው። 31አንድ ሰው ከዐሥራቱ የትኛውንም መዋጀት ቢፈልግ፣ በዋጋው ላይ አንድ አምስተኛ መጨመር አለበት። 32ከቀንድ ከብቶች፣ ከበጎችና ከፍየሎች መንጋ የሚወጣው ዐሥራት ከእረኛ በትር በታች ከሚያልፉት ዐሥረኛው እንስሳ ይሆናል፤ ይህም ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተቀደሰ ነው። 33ሰውየው መልካም የሆነውን መልካም ካልሆነው አይለይ ወይም አይተካ፤ አንዱን በሌላው ቢተካ ግን ሁለቱም እንስሳት የተቀደሱ ይሆናሉ፤ ሊዋጁም አይችሉም። 34 እግዚአብሔር (ያህዌ) በሲና ተራራ ላይ በሙሴ አማካይነት ለእስራኤል ሕዝብ የሰጣቸው ትእዛዛት እነዚህ ናቸው።