ኤርምያስ 34:14-20 NASV

14 ‘ራሱን በባርነት ለእናንተ የሸጠውን ዕብራዊ ወንድማችሁን እያንዳንዳችሁ በየሰባት ዓመቱ ነጻ ትለቃላችሁ፤ ስድስት ዓመት ከተገዛላችሁ በኋላ ነጻ ታወጡታላችሁ።’ አባቶቻችሁ ግን አልሰሙኝም ጆሮአቸውንም ወደ እኔ አላዘነበሉም።

15 እናንተም አሁን ንስሓ በመግባት በፊቴ ትክክለኛ ነገር አደረጋችሁ፤ እያንዳንዳችሁም ለወገኖቻችሁ ነጻነት ዐወጃችሁ፤ ስሜ በሚጠራበት ቤትም በፊቴ ቃል ኪዳን ገባችሁ።

16 ነገር ግን ተመልሳችሁ ስሜን አረከሳችሁ፤ ወደ ፈለጉበት እንዲሄዱ ነጻ የለቀቃችኋቸውንም ወንዶችና ሴቶች ባሪያዎቻችሁን መለሳችሁ፤ እንደ ገናም ባሪያዎቻችሁ አደረጋችኋቸው።

17 “ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ለወንድሞቻችሁና ለወገኖቻችሁ ነጻነት አላወጃችሁምና አልታዘዛችሁኝም። እንግዲህ እኔ ‘ነጻነት’ ዐውጅላችኋለሁ፤ ይላል እግዚአብሔር። ይኸውም በሰይፍ፣ በቸነፈርና በራብ የምትወድቁበት ‘ነጻነት’ ነው። ለምድር መንግሥታት ሁሉ መሠቀቂያ አደርጋችኋለሁ።

18 ኪዳኔን ያፈረሱትንና በፊቴ የገቡትን የኪዳኑን ቃል ያልፈጸሙትን ሰዎች ሥጋውን ሁለት ቦታ ከፍለው በመካከሉ እንዳለፉት፣ እንደ እንቦሳው አደርጋቸዋለሁ።

19 የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን መሪዎች፣ የቤተ መንግሥቱን ባለሟሎች፣ ካህናቱንና በእንቦሳው ሥጋ መካከል ያለፉትን ሕዝብ ሁሉ፣

20 ነፍሳቸውን ለሚሹ ጠላቶቻቸው አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ሬሳቸውም ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት መብል ይሆናል።