ኤርምያስ 34:15-21 NASV

15 እናንተም አሁን ንስሓ በመግባት በፊቴ ትክክለኛ ነገር አደረጋችሁ፤ እያንዳንዳችሁም ለወገኖቻችሁ ነጻነት ዐወጃችሁ፤ ስሜ በሚጠራበት ቤትም በፊቴ ቃል ኪዳን ገባችሁ።

16 ነገር ግን ተመልሳችሁ ስሜን አረከሳችሁ፤ ወደ ፈለጉበት እንዲሄዱ ነጻ የለቀቃችኋቸውንም ወንዶችና ሴቶች ባሪያዎቻችሁን መለሳችሁ፤ እንደ ገናም ባሪያዎቻችሁ አደረጋችኋቸው።

17 “ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ለወንድሞቻችሁና ለወገኖቻችሁ ነጻነት አላወጃችሁምና አልታዘዛችሁኝም። እንግዲህ እኔ ‘ነጻነት’ ዐውጅላችኋለሁ፤ ይላል እግዚአብሔር። ይኸውም በሰይፍ፣ በቸነፈርና በራብ የምትወድቁበት ‘ነጻነት’ ነው። ለምድር መንግሥታት ሁሉ መሠቀቂያ አደርጋችኋለሁ።

18 ኪዳኔን ያፈረሱትንና በፊቴ የገቡትን የኪዳኑን ቃል ያልፈጸሙትን ሰዎች ሥጋውን ሁለት ቦታ ከፍለው በመካከሉ እንዳለፉት፣ እንደ እንቦሳው አደርጋቸዋለሁ።

19 የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን መሪዎች፣ የቤተ መንግሥቱን ባለሟሎች፣ ካህናቱንና በእንቦሳው ሥጋ መካከል ያለፉትን ሕዝብ ሁሉ፣

20 ነፍሳቸውን ለሚሹ ጠላቶቻቸው አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ሬሳቸውም ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት መብል ይሆናል።

21 “የይሁዳን ንጉሥ ሴዴቅያስንና መኳንንቱን፣ ነፍሳቸውን ለሚሹ ጠላቶቻቸው ይኸውም ለጊዜው እናንተን ከመውጋት ለተመለሱ ለባቢሎን ንጉሥ ሰራዊት አሳልፌ እሰጣለሁ።