13 እኔ ግን እነርሱ በታመሙ ጊዜ ማቅ ለበስሁ፤ነፍሴንም በጾም አደከምኋት፤ጸሎቴም መልስ አጥቶ ወደ ጒያዬ ተመለሰ።
14 ለወዳጄ ወይም ለወንድሜ እንደማደርግ፣እየተንቈራጠጥሁ አለቀስሁ፤ለእናቴም እንደማለቅስ፣በሐዘን ዐንገቴን ደፋሁ።
15 እነርሱ ግን እኔ ስሰናከል በእልልታ ተሰበሰቡ፤ግፈኞች በድንገት ተሰበሰቡብኝ፤ያለ ዕረፍትም ቦጫጨቁኝ።
16 እንደ ምናምንቴዎች አፌዙብኝ፤ጥርሳቸውንም አፋጩብኝ።
17 ጌታ ሆይ፤ እስከ መቼ ዝም ብለህ ታያለህ?ነፍሴን ከክፉ ሥራቸው፣ብርቅ ሕይወቴን ከአንበሶች ታደጋት።
18 በታላቅ ጉባኤ መካከል አመሰግንሃለሁ፤ብዙ ሕዝብ በተሰበሰበበትም አወድስሃለሁ።
19 ከምድር ተነሥተው ጠላቶቼ የሆኑት፣በላዬ ደስ አይበላቸው፤እንዲያው የሚጠሉኝ፣በዐይናቸው አይጣቀሱብኝ።