መዝሙር

ምዕራፎች 7

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

በስደት ጊዜ የጻድቁ ሰው ጸሎት

ዳዊት በብንያማዊው በኩዝ ምክንያት ለእግዚአብሔር የዘመረው መዝሙር

1 እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ አንተ መሸሸጊያዬ ነህ፤ከሚያሳድዱኝ ሁሉ አድነኝ፤ ታደገኝም፤ 2አለበለዚያ እንደ አንበሳ ይዘነጣጥሉኛል፤የሚያድነኝ በሌለበትም ይቦጫጭቁኛል። 3 እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ ይህን አድርጌ ከሆነ፣በደልም በእጄ ከተገኘ፣ 4በጎ ለዋለልኝ ክፉ መልሼ ብሆን፣ጠላቴንም በከንቱ ዘርፌ ከሆነ፣ 5ጠላቴ አሳዶ ይያዘኝ፤ሕይወቴን ከምድር ይቀላቅል፤ክብሬንም ከዐፈር ይደባልቅ። ሴላ 6 እግዚአብሔር ሆይ፤ በመዓትህ ተነሥ፤በቍጣ በተነሡብኝ ላይ ተነሥ፤አምላኬ ሆይ፤ ንቃ፤ ትእዛዝም አስተላልፍ! 7የሕዝቦች ጉባኤ ይክበብህ፤አንተም ከላይ ሆነህ ግዛቸው፤ 8 እግዚአብሔር በሕዝቦች ላይ ይፈርዳል። እግዚአብሔር ሆይ፤ እንደ ጽድቄ ፍረድልኝ፤ልዑል ሆይ፤ እንደ ቅን አካሄዴ መልስልኝ። 9ልብንና ኵላሊትን የምትመረምር፣ጻድቅ አምላክ ሆይ፤የክፉዎችን ዐመፅ አጥፋ፤ጻድቁን ግን አጽና። 10ጋሻዬ ልዑል አምላክ ነው፤እርሱ ልበ ቅኖችን ያድናቸዋል። 11እግዚአብሔር ጻድቅ ዳኛ ነው፤ቍጣውንም በየዕለቱ የሚገልጥ አምላክ ነው። 12ሰው በንስሓ የማይመለስ ከሆነ ግን፣ሰይፉን ይስላል፤ቀስቱን ይገትራል። 13የሚገድሉ ጦር ዕቃዎቹን አሰናድቶአል፤የሚንበለበሉትን ፍላጻዎቹንም አዘጋጅቶአል። 14ክፋትን እያማጠ ያለ ሰው፣ቅጥፈትን አርግዞ፣ ሐሰትን ይወልዳል። 15ጒድጓድ ምሶ ዐፈሩን የሚያወጣ፣ባዘጋጀው ጒድጓድ ራሱ ይገባበታል። 16ተንኰሉ ወደ ራሱ ይመለሳል፤ዐመፃውም በገዛ ዐናቱ ላይ ይወርዳል። 17ስለ ጽድቁ ለእግዚአብሔር ምስጋና አቀርባለሁ፤የልዑል እግዚአብሔርን ስም በመዝሙር አወድሳለሁ።