መዝሙር 39 NASV

ታላቅ እግዚአብሔር - ታናሽ ሰው

ለመዘምራን አለቃ፣ ለኤዶታም፤ የዳዊት መዝሙር

1 እኔ፣ “በአንደበቴ እንዳልበድል፣መንገዴን እጠብቃለሁ፤ክፉዎችም በእኔ ዘንድ እስካሉ ድረስ፣ልጓም በአፌ አስገባለሁ” አልሁ።

2 እንደ ዲዳ ዝም አልሁ፤ለበጎ ነገር እንኳ አፌን ዘጋሁ፤ሆኖም ጭንቀቴ ባሰ።

3 ልቤ በውስጤ ጋለ፤በማሰላስልበትም ጊዜ እሳቱ ነደደ፤ከዚያም በአንደበቴ እንዲህ ተናገርሁ፤

4 “እግዚአብሔር ሆይ፤ የሕይወቴን ፍጻሜ፣የዘመኔንም ቍጥር አስታውቀኝ፤አላፊ ጠፊ መሆኑንም ልረዳ።

5 እነሆ፤ ዘመኔን በስንዝር ለክተህ አስቀመጥህ፤ዕድሜዬም በፊትህ እንደ ኢምንት ነው፤በእርግጥ የሰው ሁሉ ሕይወት ተን ነው። ሴላ

6 ሰው የጥላ ውልብታ ነው፤በከንቱም ይታወካል፤ለማን እንደሚሆን ሳያውቅ ሀብት ንብረት ያከማቻል።

7 “ጌታ ሆይ፤ አሁንስ ወደ ማን ልመልከት?ተስፋዬ በአንተ ላይ ነው።

8 ከኀጢአቴ ሁሉ አድነኝ፤የሰነፎች መሣለቂያ አታድርገኝ።

9 ይህን ያደረግህ አንተ ነህና፣ዝም እላለሁ፤ አፌንም አልከፍትም።

10 ክንድህን አንሣልኝ፤ከእጅህ ምት የተነሣ ደክሜአለሁና።

11 ሰዎችን ስለ ኀጢአታቸው ለመቅጣት ትገሥጻቸዋለህ፤ሀብታቸውንም ብል እንደ በላው ታደርጋለህ፤በእርግጥ ሰው ሁሉ ተን ብቻ ነው። ሴላ

12 “እግዚአብሔር ሆይ፤ ጸሎቴን ስማ፤ጩኸቴን አድምጥ፤ልቅሶዬንም ቸል አትበል፤በአንተ ፊት እኔ መጻተኛ ነኝና፤እንደ አባቶቼም እንግዳ ነኝ።

13 ላለመመለስ ከመሰናበቴ በፊት፣ዳግመኛ ደስ ይለኝ ዘንድ ዐይንህን ከላዬ አንሣ።