መዝሙር 96 NASV

እግዚአብሔር፤ ንጉሥም ዳኛም

1 ለእግዚአብሔር አዲስ ዝማሬ ዘምሩ፤ምድር ሁሉ፤ ለእግዚአብሔር ዘምሩ።

2 ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ ስሙንም ባርኩ፤ማዳኑንም ነጋ ጠባ አውሩ።

3 ክብሩን በሕዝቦች መካከል፣ድንቅ ሥራውንም በሰዎች ሁሉ ፊት ተናገሩ።

4 እግዚአብሔር ታላቅ ነውና፤ ውዳሴም የሚገባው ነው፤ከአማልክትም ሁሉ በላይ ሊፈራ ይገባዋል።

5 የሕዝብ አማልክት ሁሉ ጣዖታት ናቸው፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።

6 ክብርና ግርማ በፊቱ ናቸው፤ብርታትና ውበትም በመቅደሱ ውስጥ አሉ።

7 የሕዝቦች ወገኖች ሆይ፤ ለእግዚአብሔር ስጡ፤ክብርንና ብርታትን ለእግዚአብሔር ስጡ።

8 ለስሙ የሚገባ ክብርን ለእግዚአብሔር ስጡ፤ቍርባንን ይዛችሁ ወደ አደባባዩ ግቡ።

9 በተቀደሰ ውበት ለእግዚአብሔር ስገዱ፤ምድር ሁሉ፤ በፊቱ ተንቀጥቀጡ።

10 በሕዝቦች መካከል፣ “እግዚአብሔር ነገሠ” በሉ፤ዓለም በጽኑ ተመሥርታለች፤ አትናወጥም፤እርሱ ለሕዝቦች በእኩልነት ይፈርዳል።

11 ሰማያት ደስ ይበላቸው፤ ምድርም ሐሤት ታድርግ፤ባሕርና በውስጧ ያለው ሁሉ ያስተጋባ፤

12 መስኩና በላዩ ያለው ሁሉ ይፈንጥዝ፤ያን ጊዜ የዱር ዛፎች ሁሉ በደስታ ይዘምራሉ፤

13 እርሱ ይመጣልና በእግዚአብሔር ፊት ይዘምራሉ፤በምድር ላይ ሊፈርድ ይመጣል፤በዓለም ላይ በጽድቅ፣በሕዝቦችም ላይ በእውነት ይበይናል።