መዝሙር 73 NASV

ሦስተኛ መጽሐፍ

የፍትሕ አሸናፊነት

የአሳፍ መዝሙር

1 እግዚአብሔር ልባቸው ንጹሕ ለሆነ፣ለእስራኤል እንዴት ቸር ነው!

2 እኔ ግን እግሬ ሊሰናከል፣አዳልጦኝም ልወድቅ ጥቂት ቀረኝ።

3 ክፉዎች ሲሳካላቸው አይቼ፣በዐመፀኞች ቀንቼ ነበርና።

4 አንዳች ጣር የለባቸውም፤ሰውነታቸውም ጤናማና የተደላደለ ነው።

5 በሰዎች የሚደርሰው ጣጣ አይደርስባቸውም፤እንደ ማንኛውም ሰው መከራ አያገኛቸውም።

6 ስለዚህ ትዕቢት የዐንገት ጌጣቸው ነው፤ዐመፅንም እንደ ልብስ ተጐናጽፈዋል።

7 የሰባ ዐይናቸው ይጒረጠረጣል፤ልባቸውም በከንቱ ሐሳብ ተሞልቶ ይፈስሳል።

8 በፌዝና በክፋት ይናገራሉ፤ቀና ቀና ብለውም በዐመፅ ይዝታሉ።

9 አፋቸውን በሰማይ ላይ ያላቅቃሉ፤አንደበታቸውም ምድርን ያካልላል።

10 ስለዚህ ሕዝቡ ወደ እነርሱ ይነጒዳል፤ውሃቸውንም በገፍ ይጠጣሉ።

11 “ለመሆኑ እግዚአብሔር እንዴት ያውቃል?በልዑልስ ዘንድ ዕውቀት አለ?” ይላሉ።

12 እንግዲህ፣ ክፉዎች ይህን ይመስላሉ፤ሁል ጊዜ ግድ የለሽና ሀብት በሀብት ናቸው።

13 ለካ ልቤን ንጹሕ ያደረግሁት በከንቱ ነው፤እጄንም በየዋህነት የታጠብሁት በከንቱ ኖሮአል!

14 ቀኑን ሙሉ ተቀሠፍሁ፤ጠዋት ጠዋትም ተቀጣሁ።

15 “እኔ እንደዚህ እናገራለሁ” ብልማ ኖሮ፣የልጆችህን ትውልድ በከዳሁ ነበር።

16 ይህን ነገር ለመረዳት በሞከርሁ ጊዜ፣አድካሚ ተግባር መስሎ ታየኝ።

17 ይኸውም ወደ አምላክ መቅደስ እስክገባ፣መጨረሻቸውንም እስካይ ድረስ ነበር።

18 በእርግጥ በሚያዳልጥ ስፍራ አስቀመጥኻቸው፤ወደ ጥፋትም አወረድሃቸው።

19 እንዴት ፈጥነው በቅጽበት ጠፉ!በድንጋጤ ፈጽመው ወደሙ።

20 ሰው ከሕልሙ ሲነቃ እንደሚሆነው፣ጌታ ሆይ፤ አንተም በምትነሣበት ጊዜ፣እንደ ቅዠት ከንቱ ታደርጋቸዋለህ።

21 ነፍሴ በተማረረች ጊዜ፣ልቤም በተቀሠፈ ጊዜ፣

22 ስሜት የሌለውና አላዋቂ ሆንሁ፤በፊትህም እንደ እንስሳ ሆንሁ።

23 ይህም ሆኖ ዘወትር ከአንተ ጋር ነኝ፤አንተም ቀኝ እጄን ይዘኸኛል።

24 በምክርህ መራኸኝ፤ኋላም ወደ ክብር ታስገባኛለህ።

25 በሰማይ ከአንተ በቀር ማን አለኝ?በምድርም ከአንተ ሌላ የምሻው የለኝም።

26 ሥጋዬና ልቤ ሊደክሙ ይችላሉ፤እግዚአብሔር ግን የልቤ ብርታት፣የዘላለም ዕድል ፈንታዬ ነው።

27 እነሆ፤ ከአንተ የሚርቁ ይጠፋሉና፤አንተ ታማኞች ያልሆኑልህን ሁሉ ታጠፋቸዋለህ።

28 ለእኔ ግን ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ይሻለኛል፤ጌታ እግዚአብሔርን መጠጊያዬ አድርጌዋለሁ፤ስለ ሥራህም ሁሉ እናገር ዘንድ።