መዝሙር 21 NASV

ምስጋና ስለ ንጉሡ

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ንጉሥ በኀይልህ ደስ ይለዋል፤በምትሰጠውም ድል እጅግ ሐሤት ያደርጋል።

2 የልቡን መሻት ሰጠኸው፤የከንፈሮቹንም ልመና አልከለከልኸውም። ሴላ

3 መልካም በረከት ይዘህ በመንገዱ ላይ ጠብቀኸው፤የንጹሕ ወርቅ ዘውድም በራሱ ላይ ደፋህለት።

4 ሕይወትን ለመነህ፤ረዥም ዘመናትንም እስከ ዘላለም ሰጠኸው።

5 ባቀዳጀኸው ድል ክብሩ ታላቅ ሆነ፤ክብርንና ሞገስን አጐናጸፍኸው።

6 ዘላለማዊ በረከትን ሰጠኸው፤ከአንተ ዘንድ በሚገኝ ፍስሓም ደስ አሰኘኸው፤

7 ንጉሡ በእግዚአብሔር ተማምኖአልና፤ከልዑልም ጽኑ ፍቅር የተነሣ፣ከቆመበት አይናወጥም።

8 እጅህ ጠላቶችህን ሁሉ ታገኛቸዋለች፤ቀኝ እጅህም የሚጠሉህን ፈልጋ ትይዛለች።

9 በምትገለጥበት ጊዜ፣እሳት እንደሚንቀለቀልበት ምድጃ ታደርጋቸዋለህ፤ እግዚአብሔር በመዓቱ እንዳልነበሩ ያደርጋቸዋል፤እሳቱም ሙጥጥ አድርጋ ትበላቸዋለች።

10 ዘራቸውን ከምድር፣ዘር ማንዘራቸውንም ከሰው ልጆች መካከል ታጠፋለህ።

11 ክፋት ቢያስቡብህ፣ተንኰል ቢወጥኑብህም አይሳካላቸውም፤

12 በመጡበት ትመልሳቸዋለህና፤ቀስትህንም በፊታቸው ላይ ታነጣጥራለህ።

13 እግዚአብሔር ሆይ፤ በብርታትህ ከፍ ከፍ በል፤ኀይልህን እናወድሳለን፤ እንዘምራለንም።