መዝሙር

ምዕራፎች 143

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

ትሑት ልመና

የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ጸሎቴን ስማ፤ልመናዬን አድምጥ፤በታማኝነትህና በጽድቅህም፣ሰምተህ መልስልኝ። 2ሰው ሆኖ በፊትህ ጻድቅ የለምና፣ባሪያህን ወደ ፍርድ አታቅርበው። 3ጠላት እስከ ሞት አሳዶኛል፤ሕይወቴንም አድቅቆ ከዐፈር ቀላቅሎአል፤ቀደም ብለው እንደ ሞቱትም፣በጨለማ ውስጥ አኑሮኛል። 4ስለዚህ መንፈሴ በውስጤ ዝላለች፤ልቤም በውስጤ ደንግጦአል። 5የቀድሞውን ዘመን አስታወስሁ፤ሥራህንም ሁሉ አሰላሰልሁ፤የእጅህንም ሥራ አውጠነጠንሁ። 6እጆቼን ወደ አንተ ዘረጋሁ፤ነፍሴም እንደ ምድረ በዳ አንተን ተጠማች። ሴላ 7 እግዚአብሔር ሆይ፤ ፈጥነህ መልስልኝ፤መንፈሴ ደከመች፤ወደ ጒድጓድ እንደሚወርዱት እንዳልሆን፣ፊትህን ከእኔ አትሰውር። 8በአንተ ታምኛለሁና፣በማለዳ ምሕረትህን አሰማኝ፤ነፍሴን ወደ አንተ አንሥቻለሁና፣የምሄድበትን መንገድ አሳየኝ። 9 እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን መሰወሪያ አድርጌአለሁና፣ከጠላቶቼ አድነኝ። 10አንተ አምላኬ ነህና፣ፈቃድህን እንድፈጽም አስተምረኝ፤መልካሙ መንፈስህም፣በቀናችው መንገድ ይምራኝ። 11 እግዚአብሔር ሆይ፤ ስለ ስምህ ሕያው አድርገኝ፤በጽድቅህም ነፍሴን ከመከራ አውጣት። 12ጠላቶቼንም ለእኔ ስላለህ ምሕረት ደምስሳቸው፤እኔ ባሪያህ ነኝና፣ነፍሴን የሚያስጨንቋትን ሁሉ አጥፋቸው።