መዝሙር 143 NASV

ትሑት ልመና

የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ጸሎቴን ስማ፤ልመናዬን አድምጥ፤በታማኝነትህና በጽድቅህም፣ሰምተህ መልስልኝ።

2 ሰው ሆኖ በፊትህ ጻድቅ የለምና፣ባሪያህን ወደ ፍርድ አታቅርበው።

3 ጠላት እስከ ሞት አሳዶኛል፤ሕይወቴንም አድቅቆ ከዐፈር ቀላቅሎአል፤ቀደም ብለው እንደ ሞቱትም፣በጨለማ ውስጥ አኑሮኛል።

4 ስለዚህ መንፈሴ በውስጤ ዝላለች፤ልቤም በውስጤ ደንግጦአል።

5 የቀድሞውን ዘመን አስታወስሁ፤ሥራህንም ሁሉ አሰላሰልሁ፤የእጅህንም ሥራ አውጠነጠንሁ።

6 እጆቼን ወደ አንተ ዘረጋሁ፤ነፍሴም እንደ ምድረ በዳ አንተን ተጠማች። ሴላ

7 እግዚአብሔር ሆይ፤ ፈጥነህ መልስልኝ፤መንፈሴ ደከመች፤ወደ ጒድጓድ እንደሚወርዱት እንዳልሆን፣ፊትህን ከእኔ አትሰውር።

8 በአንተ ታምኛለሁና፣በማለዳ ምሕረትህን አሰማኝ፤ነፍሴን ወደ አንተ አንሥቻለሁና፣የምሄድበትን መንገድ አሳየኝ።

9 እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን መሰወሪያ አድርጌአለሁና፣ከጠላቶቼ አድነኝ።

10 አንተ አምላኬ ነህና፣ፈቃድህን እንድፈጽም አስተምረኝ፤መልካሙ መንፈስህም፣በቀናችው መንገድ ይምራኝ።

11 እግዚአብሔር ሆይ፤ ስለ ስምህ ሕያው አድርገኝ፤በጽድቅህም ነፍሴን ከመከራ አውጣት።

12 ጠላቶቼንም ለእኔ ስላለህ ምሕረት ደምስሳቸው፤እኔ ባሪያህ ነኝና፣ነፍሴን የሚያስጨንቋትን ሁሉ አጥፋቸው።