መዝሙር 104 NASV

የፍጥረት መብት

1 ነፍሴ ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኪ፤ እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ አንተ እጅግ ታላቅ ነህ፤ክብርንና ግርማን ለብሰሃል።

2 ብርሃንን እንደ ሸማ ተጐናጽፈሃል፤ሰማያትንም እንደ ድንኳን መጋረጃ ዘረጋህ፤

3 የእልፍኝህን አግዳሚ በውሆች ላይ አኖርህ፤ደመናትን ሠረገላህ አደረግህ፤በነፋስ ክንፍ ትሄዳለህ።

4 መላእክትህን መንፈስ፣አገልጋዮችህንም የእሳት ነበልባል ታደርጋለህ።

5 ለዘላለም እንዳትናወጥ፣ምድርን በመሠረቷ ላይ አጸናሃት።

6 በጥልቁ እንደ ልብስ ሸፈንሃት፤ውሆችም ከተራሮች በላይ ቆሙ።

7 በገሠጽሃቸው ጊዜ ግን ፈጥነው ሄዱ፤የነጐድጓድህንም ድምፅ በሰሙ ጊዜ ሸሹ።

8 በተራሮች ላይ ፈሰሱ፤ወዳዘጋጀህላቸው ስፍራ፣ወደ ሸለቆዎች ወረዱ።

9 ተመልሰው ምድርን እንዳይሸፍኑ፣አልፈውም እንዳይመጡ ድንበር አበጀህላቸው።

10 ምንጮችን በሸለቆ ውስጥ እንዲሄዱ አደረግህ፤በተራሮችም መካከል ይፈሳሉ፤

11 የዱር እንስሳትም ከዚያ ይጠጣሉ፤የሜዳ አህዮችም ጥማቸውን ይቈርጣሉ።

12 የሰማይ ወፎች ጎጇቸውን በወንዞቹ ዳር ይሠራሉ፤በቅርንጫፎችም መካከል ይዘምራሉ።

13 ከላይ ከእልፍኝህ ተራሮችህን ታጠጣለህ፤ምድርም በሥራህ ፍሬ ትረካለች።

14 ከምድር ምግብን ታወጣ ዘንድ፣ለእንስሳት ሣርን፣ለሰው ልጆች ሥራ ዕፀዋትን ታበቅላለህ፤

15 የሰውን ልብ ደስ የሚያሰኝ ወይን፣ፊቱን የሚያወዛ ዘይት፣ልቡን የሚያበረታ እህል በዚህ ይገኛል።

16 ደግሞም የእግዚአብሔር ዛፎች፣እርሱ የተከላቸውም የሊባኖስ ዝግባዎች ጠጥተው ይረካሉ፤

17 ወፎች ጎጆአቸውን በዚያ ይሠራሉ፤ሽመላ በጥዶቹ ውስጥ ማደሪያ ታገኛለች።

18 ረጃጅሙ ተራራ የዋልያ መኖሪያ፣የዐለቱም ዋሻዎች የሽኮኮ መሸሸጊያ ናቸው።

19 ጨረቃን የወቅቶች መለያ አደረግሃት፤ፀሓይም የምትጠልቅበትን ጊዜ ታውቃለች።

20 ጨለማን ታመጣለህ፤ ሌሊትም ይሆናል፤የዱር አራዊትም ሁሉ በዚህ ጊዜ ወጥተው ይራወጣሉ።

21 የአንበሳ ግልገሎች ምግብ ፍለጋ ይጮኻሉ፤የሚበሉትንም ከእግዚአብሔር ይሻሉ።

22 ፀሓይ በወጣች ጊዜም ይመለሳሉ፤በየጐሬአቸውም ገብተው ይተኛሉ።

23 ሰውም ወደ ሥራው ይሄዳል፤እስኪመሽም በተግባሩ ላይ ይሰማራል።

24 እግዚአብሔር ሆይ፤ ሥራህ እንዴት ብዙ ነው!ሁሉን በጥበብ ሠራህ፤ምድርም በፍጥረትህ ተሞላች።

25 ይህች ባሕር ሰፊና የተንጣለለች ናት፤ታላላቅና ታናናሽ እንስሳት፣ስፍር ቍጥር የሌላቸውም ነፍሳት በውስጧ አሉ።

26 መርከቦች በላይዋ ይመላለሳሉ፤አንተ የፈጠርኸውም ሌዋታን በውስጧ ይፈነጫል።

27 ምግባቸውን በወቅቱ ትሰጣቸው ዘንድ፣እነዚህ ሁሉ አንተን ተስፋ ያደርጋሉ።

28 በሰጠሃቸውም ጊዜ፣አንድ ላይ ያከማቻሉ፤እጅህንም ስትዘረጋ፣በመልካም ነገር ይጠግባሉ።

29 ፊትህን ስትሰውር፣በድንጋጤ ይሞላሉ፤እስትንፋሳቸውንም ስትወስድባቸው ይሞታሉ፤ወደ ዐፈራቸውም ይመለሳሉ።

30 መንፈስህን ስትልክ፣እነርሱ ይፈጠራሉ፤የምድርንም ገጽ ታድሳለህ።

31 የእግዚአብሔር ክብር ለዘላለም ጸንቶ ይኑር፤ እግዚአብሔር በሥራው ደስ ይበለው፤

32 እርሱ ምድርን ሲመለከት፣ ትንቀጠቀጣለች፤ተራሮችም እርሱ ሲዳስሳቸው ይጤሳሉ።

33 በሕይወት ሳለሁ ለእግዚአብሔር እዘምራለሁ፤ቆሜ እስከ ሄድሁ ድረስም አምላኬን እወድሳለሁ።

34 እኔ በእግዚአብሔር ደስ እንደሚለኝ፣የልቤ ሐሳብ እርሱን ደስ ያሰኘው።

35 ኀጥአን ከምድር ገጽ ይጥፉ፤ዐመፀኞች ከእንግዲህ አይገኙ።ነፍሴ ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኪ፤ሃሌ ሉያ።