መዝሙር 48 NASV

የእግዚአብሔር ተራራ ጽዮን

ዝማሬ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር

1 እግዚአብሔር ታላቅ ነው፤በአምላካችን ከተማ በተቀደሰው ተራራ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባዋል።

2 የምድር ሁሉ ደስታ የሆነው፣በሰሜን በኩል በርቀት የሚታየው፣በከፍታ ላይ አምሮ የደመቀው የጽዮን ተራራ፣የታላቁ ንጉሥ ከተማ ነው።

3 እግዚአብሔር በአዳራሾቿ ውስጥ ሆኖ፤ብርቱ ምሽግ እንደሆናት አስመስክሮአል።

4 እነሆ፤ ነገሥታት ተባብረው መጡ፤አንድ ላይ ሆነውም ገሠገሡ።

5 አይተውም ተደነቁ፤ደንግጠውም ፈረጠጡ።

6 ምጥ እንደ ያዛት ሴት፣በዚያ ብርክ ያዛቸው።

7 የምሥራቅ ነፋስ የተርሴስን መርከብ እንደሚሰባብር፣አንተ አብረከረክሃቸው።

8 እንደ ሰማን፣በሰራዊት አምላክ ከተማ፣በአምላካችን ከተማ፣እንዲሁ አየን፤እግዚአብሔር ለዘላለም ያጸናታል። ሴላ

9 አምላክ ሆይ፤ በቤተ መቅደስህ ውስጥ ሆነን፣ምሕረትህን እናስባለን።

10 አምላክ ሆይ፤ ምስጋናህ እንደ ስምህ፣እስከ ምድር ዳርቻ ይዘልቃል፤ቀኝ እጅህም ጽድቅን የተሞላች ናት።

11 ስለ ፍርድህ፣የጽዮን ተራራ ሐሤት ታድርግ፤የይሁዳ መንደሮችም ደስ ይበላቸው።

12 በጽዮን አካባቢ ተመላለሱ፤ ዙሪያዋንም ሂዱ፤የጥበቃ ግንበኞቿንም ቍጠሩ፤

13 ለሚቀጥለው ትውልድ ትናገሩ ዘንድ፣መከላከያ ዕርዶቿን ልብ ብላችሁ ተመልከቱ፤መጠበቂያ ማማዎቿን እዩ።

14 ይህ አምላክ ከዘላለም እስከ ዘላለም አምላካችን ነውና፤እስከ መጨረሻው የሚመራንም እርሱ ነው።